በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጀመረው አዲስ የወባ መከላከያ ክትባት፣ በደቡብ ኢትዮጵያ ቱርሚ ከተማ መተግበሩን የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል::
ለመጀመሪያ ጊዜ በኢትዮጵያ የሚሰጠው አዲሱ የወባ መከላከያ ክትባት፣ ዕድሜያቸው ከ5 ዓመት በታች ለሆኑ ህፃናት የሚሰጥ መሆኑን የገለፁት የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ፤ ክትባቱ ውጤታማ ስለመሆኑ በጥናት መረጋገጡን ዘመቻውን ባስጀመሩበት ወቅት ተናግረዋል።
ዶ/ር ደረጀ አክለውም፤ አዲሱ የወባ መከላከያ ክትባት ከመደበኛ የክትባት ፕሮግራም ጋር ተቀናጅቶ በሀገር አቀፍ ደረጃ በ58 ወረዳዎች መሰጠት እንደሚጀመር ገልፀዉ፤ ህብረተሰቡ ሌሎች የመከላከያ ዘዴዎችን አጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል።
አዲሱ የወባ መከላከያ ክትባት በክልሉ ህዝብ በተለይም ከ5 ዓመት በታች በሆኑ ህፃናት የሚደርሰውን ህመምና ሞት ለመቀነስ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል ብለዋል፡፡
የወባ ክትባት ዘመቻ ማስጀመሪያ ፕሮግራም ላይ በዓይነቱ ለየት ያለ አዲስ የመኝታ አጎበር ስርጭት የተጀመረ ሲሆን፤ 3.5 ሚሊዮን አዲስ የመኝታ አጎበር ቅድሚያ ለሚሰጣቸው የህብረተሰብ ክፍሎች የሚሰራጭ ይሆናል ተብሏል፡፡
