በኦሮሚያ ክልል ከግንቦት 04 እስከ ከግንቦት 10 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ ባሉት ቀናቶች በደረሱ የትራፊክ አደጋዎች የ18 ሰዎች ህይወት ሲያልፍ በ21 ሰዎች ላይ ከባድ 1 ሰዉ ላይ ደግሞ ቀላል የአካል ጉዳት ደርሷል፡፡
በንብረት ላይ የደረሰው ውድመት በገንዘብ ሲተመን ከአንድ ሚሊየን ሁለት መቶ ሺ ብር በላይ የሚገመት ነው።አደጋዎቹ በተለያዩ ዞኖች እና ከተሞች የተከሰቱ ናቸው።
በአንድ ሳምንት ውስጥ በደረሰ አደጋ ከ16 እስከ 52 ዓመት የእድሜ ክልል ላይ የሚገኙ ሰዎች ህይወታቸው ማለፉን የኦሮሚያ ክልል የትራፊክ ቁጥጥር ክፍል ባለሙያ የሆኑት ኢንስፔክተር መሰለ አበራ ለብስራት ሬዲዮና ቴሌቪዥን ተናግረዋል፡፡
አብዛኛዉ አደጋዎቹ የተከሰቱት በቀኑ እና በለሊቱ ክፍለ ጊዜ ሲሆን አደጋውን ያደረሱት ወንድ አሽከርካሪዎች ናቸው። የሞት አደጋዎች የደረሱት በጭነት፣ በህዝብ ማመላለሻ ፣በባለ ሦስት እግር (ባጃጅ) እና በሞተር ሳይክል የተከሰቱ መሆናቸው ተገልጿል፡፡
የአደጋዎቹ መንስኤዎቹ ከፍጥነት ወሰን በላይ ማሽከርከር እና ለእግረኛ ቅድሚያ አለመስጠት፣ የቴክኒክ ችግር ፣ለተሽከርካሪ ቅድሚያ አለመስጠት እና ርቀትን ጠብቆ አለማሽከርከር መሆኑን ኢንስፔክተር መሰለ አበራ ለብስራት ሬዲዮና ቴሌቪዥን ተናግረዋል::
