የአሜሪካው የተራድኦ ድርጅት ዩኤስኤይድ መዘጋቱን ተከትሎ በርካታ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የበጀት ችግር እንዳጋጠማቸው ተነግሯል።
ለአውሮፓውያኑ 2025 ይዘን ከነበረው በጀት ውስጥ 14 በመቶ ያህሉ በዩኤስኤይድ ድጋፍ መቋረጥ ምክንያት ተጽዕኖ ውስጥ ገብቷል ያሉት የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች ሕብረት ዋና ዳይሬክተር አቶ መስዑድ ገበየሁ፤ የተጓደለውን በጀት ለማሟላት የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን ማድረጋቸውን ጠቁመዋል።
በድርጅቱ ድጋፍ ተጀምረው የነበሩ ፕሮጀክቶች መቋረጣቸውን አክለው የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፤ የበጀት ጉድለቱን ለመቅረፍ ያካሄዱት እንቅስቃሴ ፍሬ ማፍራቱን ገልጸዋል።
በዚህም አሁን ላይ ህብረቱ በጀቱን ማሟላት መቻሉን ገልጸዋል። ሌሎች በርካታ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በመሰል ፈተና ውስጥ መሆናቸውንም የጠቆሙት አቶ መስዑድ፤ በሀገር ውስጥ ድጋፍ ማግኘት የሚቻልበትን መንገድ በማፈላለግ ዘላቂ መፍትሄ ማበጀት እንደሚገባ አመልክተዋል።
