በአልታሸጉ የወተት ምርቶች ለአደገኛ በሽታዎች የሚያጋልጡ አራት የባክቴሪያ ዓይነቶች መገኘታቸውን የኢትዮጵያ ኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ገለፀ፡፡
በኢንስቲትዩቱ የእንስሳት ነክ በሽታዎች ምርምር ዲቪዥን ኃላፊና የጸረ ተህዋስያን መድኃኒቶች ከፍተኛ ተመራማሪ ዶክተር ይመር ሙሉጌታ ለኢፕድ እንደተናገሩት፤ ማኅበረሰቡ እየተጠቀመባቸው ያሉ ያልታሸጉ ወተቶች ንጹህ ቢመስሉም በተለያየ ደረጃ ችግሮች ያሉባቸው መሆኑ ተረጋግጧል፡፡
ማኅበረሰቡ እየተጠቀመባቸው በሚገኙ የወተት ምርቶች አራት የባክቴሪያ አይነቶች ተገኝቶባቸዋል ብለዋል፡፡
ባክቴሪያዎቹ የኩላሊት፣ የሽንት መተላለፊያ እና የቆዳ በሽታን የሚያስከትሉ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ባክቴሪያዎቹ ኩላሊትንና የሽንት መተላለፊያዎችን በእጅጉ የሚጎዱ ከመሆናቸውም ባሻገር የቆዳ በሽታን የሚያስከትሉ፤ የሳምባ ምች፣ የደም ዝዉዉር እና የቁስል ኢንፌክሽኖች እና ታይፎይድን የመሳሰሉ ተላላፊ በሽታዎችን በብዛት የሚፈጥሩ እንደሆነ ጠቅሰዋል፡፡
ጥናቱ የተሠራው በማህበረሰቡ ጥቅም ላይ እየዋሉ ከሚገኙ የወተት ምርቶች ናሙና ተወስዶ እንደሆነ የጠቆሙት ተመራማሪው፤ ለጥናቱ ከፍተኛ ወተት አምራች የሆኑ ስድስት ክልሎች ናሙና መወሰዱን ተናግረዋል።
የተሰራው ጥናት በፋብሪካ የተቀነባበሩትን የወተት ተዋዕጾዎችን ያካተተ እንዳልሆነ ጠቁመዋል።
አምራቾች፣ ነጋዴዎች እና በግብርናና በጤና ዘርፍ ያሉ ባለሙያዎች እና የስራ ኃላፊዎች ከምንጊዜውም በላይ ተናበው ለመፍትሄው መረባረብ እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል ።
#Gazetteplus
