የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠ/ም/ቤት የምርጫ አስፈፃሚ ቦርድ ባለፉት ጊዜያት ሲካሄዱ የቆዩ የመጅሊስ ጠቅላላ ምርጫ ሂደትን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል።
ቦርዱ በመግለጫው ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ ምርጫው ለማካሄድ በ4 ክላስተሮች ማለትም ሰሜናዊ ክላስተር፣ደቡባዊ ክላስተር፣ምስራቃዊ ክላስተር እንዲሁም ማዕከላዊ ክላስተሮችን በመከፋፈል የተለያዩ የቅድመ ዝግጅት ስረዎች ሲያከናውን መቆየቱን ገልጿል።
በዚህም 98 በመቶ የሚሆነውን የቅድመ ምርጫ ተግባራት በማጠናቀቅ ሐምሌ 13/2017 የምዝገባ ሂደት እንደሚጠናቀቅ አስታውቋል።
ምርጫውን ለማካሄድ የሚረዱ ቅድመ ዝግጅቶች በአብዛኞቹ የሀገሪቱ አካባቢዎች ቢጠናቀቁም በተወሰኑ አካባቢዎች የምዝገባ መዘግየት መስተዋሉ የተገለፀ ሲሆን ቦርዱ ሁሉንም ካለው ተጨባጭ ሁኔታ ጋር በማገናዘብ ሂሰቱን እያስኬደ እንደሚገኝ ነው የገለፀው።
የወረዳ መጅሊስ ምክር ቤት ምስረታ በመላ ሀገሪቱ ከነሐሴ 9 እስከ 11/2017 በየመስጂዶች እንዲካሄድ መወሰኑም ነው የተመላከተው።
ከወረዳ መጅሊስ ም/ቤት ምስረታ የምርጫ ቀናት በፊት ከሐምሌ 30 እስከ ነሐሴ 4/2017 ድረስ የሙስሊሙ ማህበረሰብ ተገናኝቶ ለመጅሊስ ምርጫ የሹራ ሳምንት እንዲሆን መወሰኑም ተመላክቷል።
ቀጥሎ አርብ ነሐሴ 9 በመስጂዶች የኡለማ ዘርፍ ምርጫን ለማከናወን መወሰኑ የተገለፀ ሲሆን የምሁራንና የወጣቶች ምርጫ ነሐሴ 11 ከሰዓት በፊት፣ በዚያው እለት ከሰዓት በኋላ ሴቶችና የሰራተኛ ክፍሉ ምርጫቸውን በየመስጂዶች ምርጫቸውን ያካሂዳሉ ተብሏል።
