ኔትፍሊክስ ከናሳ ጋር በመተባበር በቅርብ ጊዜ ውስጥ የጠፈር ተመራማሪዎች በጠፈር ላይ የሚያደርጉትን ጉዞ እና ሌሎች እንቅስቃሴዎችን ማስተላለፍ ሊጀምር ነው።
የጠፈር ሮኬቶች ሲወነጨፉ እንዲሁም ከጠፈር ላይ የምድርን ገጽታን እይታ የሚያሳዩ ፕሮግራሞችንም እንደሚያስተላልፍ ኔትፍሊክስ በኤክስ ገጹ ላይ አስታውቋል።
የናሳ ዋና ስራ አስኪያጅ ሬቤካ ሲርሞንስ ስለ ፕሮግራሙ ሲገልፁ እ.አ.አ. በ1958 በተቀመጠው ሕግ መሰረት የጠፈር ላይ ጉዞዎችን እና ግኝቶችን ለሰፊው ሕዝብ እንድናጋራ የሚረዳ ሕግ አለን ብለዋል።
በተጨማሪም ለአዲሱ ትውልድ መነሳሳትን የሚፈጥርና አዝናኝ የሕዋ ፕሮግራሞች እንደሚቀርቡም ተናግረዋል።
ሰዎች ከቤታቸው ሆነው በቀላሉ እጃቸው ላይ ባለው ስልክም ፕሮግራሞቹን እንዲያገኙ እና እንዲመለከቱት ያስችላል ብለዋል።
ኔትፍሊክስ በዓለም ላይ ከ700 ሚሊዮን በላይ ተመልካች ያለው ሲሆን፤ የአሁኑ ስምምነት ብዙ ሰዎች የሕዋ ጉዳዮችን በቀጥታ እንዲመለከቱ ያስችላል ተብሏል።
