ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥ እንደሚከፈት እና በወሽመጡ የሚያልፉ መርከቦች ላይ ጥቃት እንደማታደርስ በይፋ ቃል እንድትገባ እንደምትፈልግ አሜሪካ አስታወቀች።
የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ማንነታቸው ያልተገለጸ ባለሥልጣንን ጠቅሰው እንደዘገቡት፤ ቴህራን ለፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አማካሪዎች በግል በሰጠችው ማብራሪያ መርከቦች ላይ መተኮሷ ስህተት መሆኑን አምናለች።
ኢራን ጥቃቱ የተፈጸመው ከቁጥጥር ውጭ በሆኑ ውስጣዊ ኃይሎች መሆኑን አስታውቃለች።
ባለፉት ቀናት የተኩስ ልውውጥ ቢያደርጉም ሁለቱም ወገኖች ንግግራቸውን ለመቀጠል መስማማታቸውን ትራምፕ ተናግረዋል።
ኢራን እና አሜሪካ የፈረሙት የመግባቢያ ሰነድ፤ ቴህራን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ደኅንነታቸው እንዲጠበቅ ታደርጋለች።
ከሰሞኑ የተነሳው ግጭት የመግባቢያ ሰነዱን ያፈረሰ መሆኑን ሁለቱም አገራት ገልጸዋል።
በኢራን እና በአሜሪካ መካከል የሚደረገው ድርድር እንዲቀጥል መስማማታቸውን የገለጹት ትራምፕ፤ ቀደም ሲል የነበረው የተኩስ አቁም ስምምነት ግን ማብቃቱን ለቴህራን ማሳወቃቸውን ተናግረዋል።
ቴህራን በመሠረተ ልማቶቿ ላይ ጥቃት የሚፈጸም ከሆነ አጸፋውን እንደምትመልስ አስጠንቅቃለች።
