የኢራን ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን የሆነው ኢርና ቴህራን አሜሪካ ጦርነቱን ለማቆም ላቀረበችው ምክረ ሃሳብ ምላሽ መስጠቷን ዘገበ።
እንደ ኢርና ዘገባ ከሆነ ኢራን የቀረበላትን የተኩስ አቁም ጥሪ በቋሚነት ጦርነቱን ማቆም አስፈላጊ ነው በሚል ውድቅ አድርጋለች።
የኢራን መገናኛ ብዙኃን ቴህራን አሜሪካ ላቀረበችው የተኩስ አቁም ምክረ ሃሳብ ምላሿን በፓኪስታን በኩል ማስገባቷን ዘግበዋል።
የዜና ወኪሉ ኢራን ለአሜሪካ ያቀረበችው ባለ አስር ነጥብ ምላሽ የተኩስ አቁምን ውድቅ የሚያደርግ እና በቋሚነት ጦርነቱን ለማቆም ፍላጎት መኖር አለበት የሚል መሆኑን ዘግቧል።
ኢራን ለአምስት ሳምንታት የዘለቀው ጦርነት ሙሉ በሙሉ እንዲቆም በመጠየቅ የሆርሙዝ ወሽመጥን እንድትከፍት የቀረበላትን የተኩስ አቁም ጥሪ ውድቅ አድርጋለች።
ኢራን ለአሜሪካ በሰጠችው ምላሽ ውስጥ “በቀጣናው ያለው ጦርነት እንዲቆም ፣ በሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ ውስጥ ደኅንነቱ የተጠበቀ መንገድን የሚያረጋግጥ አሰራር እንዲኖር፣ እንዲሁም መልሶ ግንባታ እና ማዕቀቦችን ማንሳትን እንዲካተቱ” የሚሉ ፍላጎቶቿን ዘርዝራለች።
ኢርና የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “በተደጋጋሚ የጊዜ ገደብ በማራዘም ከቀድሞ ዛቻዎቻቸው ወደ ኋላ ማፈግፈጋቸውን” አክሎ ዘግቧል።
ትራምፕ እስከ ማክሰኞ ዕለት ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን የማትከፈት ከሆነ በቴህራን ላይ “ሲኦል” ይወርዳል ሲሉ “ድልድዮችን እና የኃይል ማመንጫዎችን” እንደሚያጠቁ ዝተዋል።
