ኢራን፤ ዲዬጎ ጋርሺያ በተባለው የአሜሪካ እና የዩናይትድ ኪንግደም ጋራ የጦር ሰፈር ላይ ሁለት መካከለኛ ርቀት ተወንጫፊ ባለስቲክ ሚሳዔሎችን መተኮሷን የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።
ዎል ስትሪት ጆርናል ጋዜጣ በርካታ ምንጮችን ጠቅሶ ባወጣው ዘገባ፤ የተተኮሱት ሁለቱም ሚሳዔሎች በሕንድ ውቅያኖስ ላይ የሚገኘውን ጦር ሰፈር እንዳልመቱት አስታውቋል።
ሴኤንኤን በበኩሉ፤ ሚሳዔሎቹ የተተኮሱት በአካባቢው ሰዓት አቆጣጠር አርብ ንጋት ላይ እንደሆነ ከአሜሪካ ባለሥልጣን መስማቱን ዘግቧል።
ከኢራን እስከ ዲዬጎ ጋርሺያ ያለው ርቀት 3,800 ኪሎ ሜትር ገደማ ነው። የቀድሞው ኢራን ጠቅላይ መሪ የአገሪቱ ሚሳዔል የሚወነጨፍበት ርቀት ከ2,000 እንዳይበልጥ ትዕዛዝ ሰጥተው ነበር።
ቢቢሲ ስለ ጥቃቱ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት ለአሜሪካ ፔንታገን እና ለዩናይትድ ኪንግደም መከላከያ ሚኒስቴር ጥያቄ አቅርቧል። የአሜሪካው መከላከያ ሚኒስቴር ፔንታጎን “በአሁኑ ሰዓት ማቅረብ የሚችለው ምንም ነገር እንደሌለ” ገልጿል።
