ኢትዮጵያ እና ሩዋንዳ ያላቸውን ታሪካዊ የሁለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ በማጠናከር፣ የመከላከያ ዘርፉን በዘመናዊ የሰው ሠራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) ቴክኖሎጂ የታገዘ ለማድረግ መግባባት ላይ ደርሰዋል።
የኢትዮጵያ መከላከያ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሐመድ ከሩዋንዳ መከላከያ ቃል አቀባይ ብርጋዴር ጄኔራል ሮናልድ ሪቪዋንጋ ጋር በነበራቸው ውይይት፣ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የቆየ ወታደራዊ ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር መክረዋል።
በውይይቱ ወቅት ሁለቱም ወገኖች ወቅታዊ የደህንነት ተግዳሮቶችን ለመቋቋም ወታደራዊ ተግባራትን በቴክኖሎጂ ማዘመን ወሳኝ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። በተለይም ወታደራዊ ስምሪቶችን በፈጣንና በዘመናዊ መንገድ መምራት፤ የደህንነት ስጋቶችን ቀድሞ ለመተንበይና ለመተንተን የሰው ሠራሽ አስተውሎትን መጠቀም፤ የላቁ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የሀገራቱን የመከላከል አቅም ማጎልበት በሚሉ ነጥቦች ላይ የጋራ መግባባት ተፈጥሯል።
ይህ አዲስ የትብብር አቅጣጫ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ወታደራዊ ዲፕሎማሲ ከማጠናከሩ ባለፈ፣ ለአፍሪካ ቀንድና ለምስራቅ አፍሪካ ቀጠናዊ ሰላምና ደህንነት ትልቅ ፋይዳ እንደሚኖረው ታምኖበታል።
