በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት 61ኛው መደበኛ ስብሰባ ላይ ኢትዮጵያ እና ብሩንዲ በምዕራባውያን አገራት አነሳሽነት የቀረበውን የዩክሬን የውሳኔ ሃሳብ በመቃወም ድምፅ ሰጥተዋል።
በጄኔ በተካሄደው በዚህ ስብሰባ ላይ የቀረበው ሰነድ በዩክሬን ያለውን የሰብዓዊ መብት ሁኔታ የሚከታተለው ዓለም አቀፍ መርማሪ ኮሚሽን የሥራ ዘመን ለተጨማሪ አንድ ዓመት እንዲራዘም የሚጠይቅ ቢሆንም፣ ኢትዮጵያን ጨምሮ ኩባ ፣ ቻይና እና ብሩንዲ የውሳኔ ሃሳቡን ውድቅ አድርገውታል።
ምንም እንኳን የውሳኔ ሃሳቡ በዋናነት በኔቶ እና በአውሮፓ ህብረት አባል አገራት ድጋፍ ቢጸድቅም፣ እንደ ኬንያ፣ ግብፅ፣ አንጎላ እና ደቡብ አፍሪካ ያሉ 18 አገራት ድምፅ ከመስጠት ተቆጥበዋል።
የውሳኔ ሃሳቡ ይዘት ሩሲያ ወታደሮቿን ከዩክሬን እንድታስወጣ የሚጠይቅና የዩክሬንን የግዛት አንድነት የሚያረጋግጥ ሲሆን፣ ሩሲያ በበኩሏ የምርመራ ኮሚሽኑን “አድሏዊ እና ፖለቲካዊ ዓላማ ያለው ነው” በማለት ስትቃወም ቆይታለች።
