ከአሜሪካ እና የእስራኤል ጥቃት ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ ሰባት ሚሊዮን ኢራናውያን አገራቸውን ለመከላከል በፈቃደኝነት ለወታደራዊ አገልግሎት ከሠራዊቱ ጎን መሰለፋቸውን የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ ሞሐማድ ባግሄር ጋሊባፍ ተናገሩ።
አፈ ጉባኤው የአገሪቱ መንግሥት ባካሄደው “ከፍተኛ ብሔራዊ ዘመቻ” በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢራናውያን “ታጥቀው አገራቸውን ለመከላከል ቁርጠኝነታቸውን አሳውቀዋል” ብለዋል።
“ከዚህ በፊትም አድርገነዋል፤ አሁንም ልንደግመው ዝግጁ ነን. . . መላውን ኢራናውያንን ነው የምትገጥሙት” በማለት እስራኤል እና አሜሪካንን “ሞክሩት” ብለዋቸዋል።
በኢራን መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ ተሰሚነት ያቸላው አፈ ጉባኤው ይህንን ያሉት ፕሬዝዳንት ትራምፕ እየተካሄደ ያለው የድርድር ጥረት ውጤት ካላስገኘ በቀጣዮቹ ጥቂት ሳምንታት በሚፈጸሙት ጥቃቶች “ኢራን ከፍተኛ ውድመት” ይገጥማታል ብለው ካስጠነቀቁ በኋላ ነው።
አሁን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢራናውያን ጠመንጃ በማንሳት ጠላትን ሊፋላሙ እንደተዘጋጁ የገለጹት አፈ ጉባኤ ሞሐማድ ባግሄር ጋሊባፍ በኢራን መንግሥት ውስጥ ለመነጋገር የሚሆኑ ሰው እና ቀጣዩ የአገሪቱ መሪ ይሆናሉ እያለች አሜሪካ በተደጋጋሚ የምትጠቅሳቸው ባለሥልጣን ናቸው።
በተጨማሪም የኢራን ጦር አዛዥ ሜጀር ጄነራል አሚር ሃታሚ፤ የአገሪቱ ሠራዊት የሚሰነዘር የጠላት ጥቃትን ለመከላከል እና አስፈላጊውን እርምጃ ለመውሰድ ዝግጁ እንዲሆን አዝዘዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በኢራን ላይ የሚፈጸመው ጥቃት በዛሬው ዕለትም የቀጠለ ሲሆን፣ ከቴህራን በስተምዕራብ የምትገኘው ካራጅ ከተማ “ክፉኛ መመታቷን” እና በከተማዋ የሚገኝ ቁልፍ ድልድይ ዒላማ መደረጉን ምንጮች ለቢቢሲ የፋርስ ቋንቋ ተናግረዋል።
በተመሳሳይ ሳዑዲ አረቢያ እና የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ፣ ኢራን ሚሳዔሎች እና ድሮኖችን ወደ ግዛቶቻቸው ማስወንጨፍ መቀጠሏን አስታውቀዋል።
