የኢትዮጵያ መከላከያ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሀመድ በቼክ ሪፐብሊክ ፕራግ በመገኘት ከሀገሪቱ የመከላከያ ሚኒስትር ጃና ሴሬንኮቫ ጋር በሁለትዮሽ ጉዳዮች ላይ ውይይት ማድረጋቸውን መከላከያ ሚኒስቴር አስታወቀ።
የሁለትዮሽ ውይይቱ የተካሄደው ከዚህ ቀደም በህዳር ወር 2016 ዓ/ም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ወደ ፕራግ በማምራት ከቼክ ሪፐብሊክ መሪ ጋር በተገናኙበት ወቅት የተግባቡባቸውን ስትራቴጂካዊ ጉዳዮች መሰረት በማድረግ ነው።
በጉብኝቱ ወቅት ጠ/ሚ አብይ ወታደራዊ አውሮፕላኖችን በማሻሻል በጥገና እና በመከላከያ ምርምር ላይ የተሰማራ ቀዳሚ የቼክ ሪፐብሊክን ተቋም ጎብኝተዋል።
በወቅቱ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ባወጣው መግለጫ ሁለቱ አገራት በመከላከያ ዘርፍ “የካበተ ልምድን ማጋራት እና በአቅም ግንባታ ላይ መግባባት ላይ ደርሰዋል” ብሏል።
እንደ ብርኖ ዴይሊ ዘገባ የቼክ ሪፐብሊክ ጠቅላይ ሚኒስትር ፔትር ፊያላ እና ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ የመከላከያ እና ደህንነትን ጨምሮ በሌሎች መስኮች ላይ ትብብር ለማድረግ መክረዋል።
የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሀመድ ወደ ፕራግ ያደረጉት ጉብኝት እነዚህን የጋራ መግባባት ላይ የተደረሰባቸውን ስምምነቶች ወደላቀ ደረጃ ለማሳደግ እና የሁለትዮሽ ወታደራዊ ትብብርን ለማጠናከር ያለመ ነው።
በውይይቱ ሁለቱ አገራት በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በመከላከያ ኢንዱስትሪ በኤሮሜዲካል ድጋፍና ጥገና እንዲሁም በስልጠናና አቅም ግንባታ መስኮች የሚያደርጉትን ትብብር ለማሳደግ የተስማሙ ሲሆን አጋርነታቸውን ለማጠናከርና የጋራ ተጠቃሚነትን ለማስፋትም ተስማምተዋል ሲል የመከላከያ ሚኒስቴር ፅህፈት ቤት ገልጿል።
ፎቶ፡ የመከላከያ ሚኒስቴር
