የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) የካቲት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ባወጣው መግለጫ፣ በኢትዮጵያ ላይ “የጦርነት ደመና” እያንዣበበ መሆኑን በመጥቀስ፤ ባለፉት አሥር ዓመታት በኦሮሚያ እና በሌሎች አካባቢዎች የቀጠሉት ግጭቶች ለአገሪቱ የጸጥታ፣ የማኅበራዊ እና የኢኮኖሚ ቀውስ ዋነኛ መንስዔ ሆነው መቀጠላቸውን አስታወቀ።
የአገሪቱን የጸጥታ ሁኔታ በተመለከተ መግለጫ የሰጠው ኦነግ፣ የፖለቲካ ልዩነቶች አሁንም መፍትሔ አለማግኘታቸውን ገልጿል። በመሆኑም በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚኖሩ የኦሮሞ ሕዝብ እና የኦሮሚያ ነዋሪዎች የክልላቸውን ወሰን እንዲጠብቁ እና አንድነታቸውን እንዲያጠናክሩ ጥሪ አቅርቧል። ድርጅቱ ይህንን ማድረግ እንደ አንድ ዜጋ የሲቪክ ግዴታ መሆኑንም አጽንኦት ሰጥቷል።
በኢትዮጵያ ውስጥ የሚካሄደው የትጥቅ ግጭት መቀጠሉን የጠቀሰው መግለጫው፣ “ታሪካዊ የኦሮሞ መሬት ዝርፊያ” አሁንም አልቆመም ሲል ከሷል።
እንደ ኦነግ ገለጻ፣ ኦሮሚያ በተፈጥሮ ሀብት የበለጸገች ብትሆንም፣ ለረጅም ጊዜ የዘለቁ ግጭቶች ክልሉን ተደጋጋሚ የጦርነት እና የብዝበዛ መድረክ አድርገውታል፤ በዚህም ምክንያት በርካታ ነዋሪዎች ለከፍተኛ የኢኮኖሚ ችግር ተጋልጠዋል።
ባለፉት ጥቂት ዓመታት የኦሮሚያን ድንበር አቋርጠው የሚገቡ የትጥቅ እንቅስቃሴዎች የአካባቢውን የጸጥታ ሁኔታ ይበልጥ እንዳባባሱት ፓርቲው ገልጿል። ይህ ሁኔታ በአንዳንድ አካባቢዎች የአስተዳደር ቁጥጥር እንዲላላ እና የሲቪል ዜጎች የዕለት ተዕለት ሕይወት እንዲስተጓጎል ማድረጉንም አክሎ ገልጿል።
ኦነግ ለዚህም መፍትሔ ይሆን ዘንድ መንግሥት ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር እውነተኛ እና ሁሉን አቀፍ የፖለቲካ ውይይት እንዲጀምር ጠይቋል።
በተጨማሪም የዲሞክራሲያዊ እና የሰብዓዊ መብቶች መከበር እንዲረጋገጥ፣ እንዲሁም የክልል ወሰን ክርክሮች በድርድር እና በሕጋዊ ማዕቀፎች እንዲፈቱ አሳስቧል። ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን በሚደረገው ጥረት ውስጥ የአገር ውስጥ እና የዓለም አቀፍ ተዋናዮች ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑንም አፅንኦት ሰጥቷል።
መግለጫው በማጠቃለያው፤ የፖለቲካ ኃይሎች፣ የሲቪል ማኅበራት፣ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች እና ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በኢትዮጵያ ውስጥ ዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት እንዲሰፍን የድርሻቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርቧል።
