የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ፣ የቺልድረን ኢንቨስትመንት ፈንድ ፋውንዴሽን (CIFF) ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኬቲ ሃምፕተን እና የሥራ ባልደረቦቻቸውን በዛሬው ዕለት በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።
ከንቲባዋ እና የፋውንዴሽኑ አመራሮች በጋራ በመሆን የ”ለነገዋ” የሴቶች ተሃድሶና ክህሎት ማበልፀጊያ ማዕከልን የጎበኙ ሲሆን፣ በማዕከሉ ውስጥ እየተከናወኑ ያሉ የልማትና የድጋፍ ሥራዎችን ተመልክተዋል።
ከንቲባዋ እና ኬቲ ሃምፕተን በማዕከሉ የሚገኙ ሴቶች የሚያገኟቸውን የስልጠና እና የተሃድሶ አገልግሎቶች በቅርበት መርምረዋል። በጉብኝቱ ወቅት በቀጣይ በጋራ ሊሰሩባቸው በሚገቡ የትኩረት መስኮች ላይ ሰፊ ውይይት መደረጉን ከንቲባዋ ገልጸዋል።
ፋውንዴሽኑ በሴቶች አቅም ግንባታ እና በክህሎት ማበልፀጊያ ዘርፎች ላይ ያለውን አጋርነት ይበልጥ ለማጠናከር መግባባት ላይ ተደርሷል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፣ ውይይቱ እጅግ ውጤታማ እንደነበርና ለሴቶች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
