የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን፤ የሁለተኛው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት አካል የሆነውን ከሳር ቤት – ጀርመን አደባባይ – ለቡ – ኃይሌ ጋርመንት ኮሪደር ግንባታ በፍጥነት ለማጠናቀቅ በከፍተኛ ርብርብ ላይ እንደሚገኝ አስታውቋል።
በመሆኑም ለግንባታ ሥራው ቅልጥፍና ሲባል ከነሐሴ 19 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ የግንባታ ሥራው እስኪጠናቀቅ ድረስ ከጀርመን አደባባይ እስከ ኃይሌ ጋርመንት ያለው የቀለበት መንገድ ክፍል በከፊል ለትራፊክ ዝግ ይደረጋል፡፡
በዚህም ከሳር ቤት – ጀርመን አደባባይ – ለቡ – ኃይሌ ጋርመንት ኮሪደር ግንባታ ስራ እስኪጠናቀቅ ድረስ ከአየር ጤና ወደ ጋርመንት እና ለቡ የሚጓዙ አሽከርካሪዎች፤ በጀሞ ሚካኤል አድርጎ ወደ ፉሪ አደባባይ ጋርመት የሚወስደውን መንገድ ሊጠቀሙ ይገባል ተብሏል ።
በተጨማሪም ከሣር ቤት መካኒሳ ወደ ጋርመንት እና ለቡ የሚጓዙ አሽከርካሪዎች ደግሞ በጀሞ ሚካኤል ወደ ፉሪ አደባባይ ጋርመት የሚወስደውን መንገድ መገልገል ይችላሉ።
በሌላ በኩል ከቄራ በጎፋ ወደ ጋርመት እና ለቡ የሚጓዙ አሽከርካሪዎች ደግሞ በጎፋ መብራት ኃይል ላፍቶ የሚወስደውን መንገድ ሊጠቀሙ ይገባል ሲሉ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ምክትል ኃላፊ አቶ እያሱ ሰለሞን ለብስራት ሬዲዮ ተናግረዋል ።
ከማሠልጠኛ እና ሠፈራ ወደ ጀሞ ሚካኤል እና አየር ጤና የሚጓዙ አሽከርካሪዎች በሀጫሉ መንገድ ወደ ፉሪ አደባባይና ጀሞ የሚወስደውን አማራጭ መንገድ በመጠቀም ለግንባታ ሥራው መፋጠን የተለመደውን ትብብር እንዲያደርጉ ባለሥልጣን መስሪያቤቱ አሳስቧል፡፡
በሳምራዊት ስዩም
#ዳጉ_ጆ
