የአማራ ብሔራዊ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንት ልዩ አማካሪ የሆኑት ረዳት ፕሮፌሰር ወርቁ ያዜ እንዳሉት ከሆነም ምንም እንኳን የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የወንጀል ሕግ ስለወሲባዊ ጥቃቶች የሚደነግጉ ድንጋጌዎችን የያዘ ቢሆንም፣ ችግሩን ከስር መሰረቱ ለመቅረፍ በሚያስችል ሁኔታ ምላሽ ሰጥቷል ለማለት የማያስችል መሆኑን በመጥቀስ፣ የሕግ ማዕቀፎቹን የመከለስ ጉዳይ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል መባሉን ብስራት ሬዲዮ ሰምቷል፡፡
ወሲባዊ ጥቃቶችን የሚመለከቱ የወንጀል ድርጊቶች እየተበራከቱ የመጡ ቢሆንም የወንጀል ፍትሕ አስተዳደር ሥርዓቱ የችግሩን አሳሳቢነት ግምት ውስጥ ያስገባ ምላሽ እየሰጠ ነው ለማለት አያስደፍርምም ብለዋል።
ወሲባዊ ጥቃቶችን የሚመለከቱ የወንጀል ድርጊቶችን በሚመለከት የሚደረጉ ምርመራዎች ፈጣን አለመሆን፣ ምርመራው ልዩ እውቀት ባላቸው ሰዎች አለመከናወኑ እንዲሁም ዘመናዊ ምርመራ አለመከናወኑን እንደችግር ይነሳልም ብለዋል፡፡
የአቃቤ ህግ የክስ አቀራረብ ሂደት እና የፍርድ ቤቶች የሙግት አመራር ሂደት ቀልጣፋ እና ተጎጂ ተኮር አለመሆኑንም አክለዋል፡፡
ተጎጂ ተኮር የወንጀል ፍትሕ አስተዳደር ስርዓት ሊዘረጋ ይገባል ሲባል የተከሳሽን መብት የሚያጣብብ የፍትሕ አስተዳደር ሥርዓት ማለት አለመሆኑንም ያብራሩት አማካሪው ይልቁንም የወንጀል ፍትሕ አስተዳደር ሥርዓቱ በአንድ በኩል የተጎጂዎችን ጥቅምና ፍላጎት ግምት ውስጥ ያስገባ እና ተጎጂዎችን የሚክስ በሌላ በኩል ደግሞ የተከሳሽን ንጹህ ሆኖ የመገመት መብትን ያገናዘበ የወንጀል ፍትሕ አስተዳደር ሥርዓት ማለት እንደሆነ ልብ ሊባል ይገባል ሲሉ ገልጸዋል፡፡
