አሜሪካ እንዲሰጣት በምትጠይቀው ጥበቃ የሚፈልጉ መረጃዎች ምክንያት ዚምባብዌ ከአሜሪካ 376 ሚሊዮን ዶላር የሚያስገኝላትን የጤና ስምምነት ውድቅ አደረገች።
ይህ የዚምባብዌ ውሳኔ ይፋ የሆነው ፕሬዝዳንት ኤመርሰን ምናንጋግዋ ስምምነቱ ለአሜሪካ ያደላ ነው ያሉበት የመንግሥት ማስታወሻ ሾልኮ ከወጣ በኋላ ነው።
የመንግሥት ቃል አቀባይ ኒክ ምናንግዋ በስምምነቱ አሜሪካ የጤና ናሙናዎችን ለምርምር እና ለንግድ አገለግሎት መጠየቋን እና ነገር ግን ወደ ፊት ለሚሰሩ ክትባቶች እና መድኃኒቶች ለማጋራት ፈቃደኛ አይደለችም ብለዋል።
በዚህም ሳቢያ አሜሪካ ለዚምባብዌ የምትሰጠውን የጤና ድጋፍ ለማቋረጥ እንደምትገደድ በአገሪቱ የአሜሪካ አምባሳደር ፓሜላ ትሬሞንት ባወጡት መግለጫ አሳውቀዋል።
ባለፉት ሁለት ዓመታት አሜሪካ ለዚምባብዌ ከ1.9 ቢሊዮን ዶላር በላይ የሚሆን የጤና ድጋፍ ስታደርግ መቆየቷን ኤምባሲዋ ገልጿል።
ፕሬዝዳንት ትራምፕ ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ በአሜሪካ የእርዳታ አቅርቦት ላይ ባደረጉት ለውጥ የተዋወቀው አዲሱ አሠራር አገራት ጠቃሚ የጤና መረጃዎችን ለአሜሪካ በማጋራት የተለያየ መጠን ያለው ድጋፍን እንዲያገኙ የሚያደርግ ነው።
እስካሁን ኢትዮጵያን ጨምሮ 16 የአፍሪካ አገራት ከ18 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገንዘብ የሚያስገኝላቸውን ስምምነት የፈረሙ ሲሆን፣ ነገር ግን በሚተላለፈው መረጃ እና አገራት በሚያገኙት ጥቅም ላይ ጥያቄ እየተነሳ ነው።
ስምምነቱን ቀድማ የፈረመችው ኬንያ ውስጥ ያሉ የመብት ተሟጋች ቡድኖች የዜጎች ግላዊ የጤና መረጃ ለአሜሪካ ተላልፎ መሰጠቱን እንደ ስጋት በመጥቀስ ባቀረቡት ክስ ስምምነቱ በአገሪቱ ከፍተኛ ፍርድ መታገዱ ይታወሳል።
BBC
