የገንዘብ ሚኒስቴር ኢትዮጵያ ያለባትን የውጭ ብድር መጠን በተመለከተ የወጡ የተሳሳቱ ዘገባዎችን አስተባብሏል። ሚኒስቴሩ እንደገለጸው፣ እ.ኤ.አ እስከ 2024 መጨረሻ ድረስ የኢትዮጵያ የውጭ ብድር መጠን የመንግሥት ልማት ድርጅቶችን ጨምሮ 31.6 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ሲሆን፣ የሀገር ውስጥ ብድር ክምችት ደግሞ 2.3 ትሪሊዮን ብር ደርሷል ብሏል።
ባለፈው ሳምንት በኢትዮጵያ ኢኮኖሚክስ ማህበር የወጣውን ሪፖርት በማጣቀስ፣ “እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ያለበት የውጭ ዕዳ መጠን ከ575 ዶላር መድረሱ ተነገረ” በሚል ርዕስ የወጣው ዘገባ ላይ ግድፈቶች እንዳሉ የገንዘብ ሚኒስቴር ገልጿል። ዘገባው ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ እስከ 2023 ድረስ የነበራትን የውጭ ዕዳ መጠን 28.5 ቢሊዮን ዶላር ሆኖ ሳለ 62.5 ቢሊዮን ዶላር በማለት ማቅረቡ የተሳሳተ መሆኑን ሚኒስቴሩ አብራርቷል።
ሚኒስቴሩ ባወጣው መግለጫ፣ የኢትዮጵያ የውጭ ብድር በአብዛኛው የተጠራቀመ ውርስ ዕዳ (legacy debt) መሆኑን ጠቁሞ፣ መንግሥት ባለፉት ሰባት ዓመታት ይህንን የክፍያ ጫና ለመቀነስ ጥረቶችን ሲያደርግ መቆየቱን አስታውቋል።
