የመምህራን ብቃትና ተነሳሽነትን ማጎልበት ለትምህርት ጥራት ወሳኝ ሚና ያለው መሆኑን ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።
በ2ኛው ዙር የመምህራንና የትምህርት አመራሮች የአቅም ግንባታ ስልጠና መክፈቻ መርሀግብር ተካሂዷል።
በመድረኩ ላይ የትምህርት ሚኒስቴር አጠቃላይ ትምህርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ አየለች እሸቴ እንደገለፁት፤ መምህራን ተማሪዎች በብቃት፣በእውቀት ብሎም በስነምግባር በማፍራት ረገድ ሀላፊነት አለባቸው።
የመምህራንን ብቃት ማጎልበት ለትምህርት ጥራት ወሳኝ ሚና ስላለው በስልጠና አቅም ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል።
በ2ኛው ዙር ስልጠናው ከዛሬ ጀምሮ እስከ ሀምሌ 18 ቀን 2017 እንደሚካሄድ ገልጸው ከስልጠና የላቀ ውጤት የሚጠበቅ መሆኑን ተናግረዋል።
የኮተቤ ትምህርት ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንት ብርሃነመስቀል ጠና(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ እንደሀገር የተከሰተውን የትምህርት ስብራት ለመጠገንና የትምህርት ጥራት ለማሻሻል መምህራን የማይተካ ሚና አላቸው።
የትምህርት ሰርአት የመፈጸም አቅምን ለማጎልበትም የመምህራንና ትምህርት አመራሮች ስልጠና ይካሄዳል።
በዘንድሮ ክረምትም 80 ሺህ መምህራንና የትምህርት ቤት አመራሮች ስልጠና የሚሰጥ መሆኑን ተናግረዋል።
ስልጠናው የትምህርት አይነት ይዘትና የማስተማር ስነዘዴ፣ የትምህርት ቴክኖሎጂ እና የአእምሮ ጤና ስነ ልቦናና ማህበራዊ ድጋፍ ላይ ያተኮረ መሆኑንም አስታውቀዋል።
በ2016 ዓ.ም 60 ሺህ ለሚጠጉ መምህራንና ትምህርት ቤት ስልጠና የተሰጠ መሆኑን አስታውሰው፤ ይህ መርሀግብር የበቁ መምህራን በማፍራት እንደሀገር የትምህርት ጥራትን ለማብቃት የሚያስችል መሆኑን ገልፀዋል።
ጋዜጣ_ፕላስ
