የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አምስት የምርጫ ክልሎች ከትግራይ ክልል ውጭ ሆነው ለብቻቸው በቀጥታ ለሕዝብ ተወካዮች ምከር ቤት ምርጫ እንዲደረግ ያስተላለፈውን ውሳኔ በጽኑ ተቃወመ። አስተዳደሩ ይህ እርምጃ ሕገ-መንግሥቱን የሚጥስና እና የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት አደጋ ላይ የሚጥል ነው ሲል አስጠንቅቋል።
የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዝዳንት ጽሕፈት ቤት ባወጣው መግለጫ፣ የትግራይ ሕዝብ ከሌሎች ጭቆና ከደረሰባቸው ሕዝቦች ጋር በመሆን “በመራራ ትግል እና በከፍተኛ መስዋዕትነት” የኢትዮጵያን ፌዴራላዊ ሥርዓት ለመመሥረት ግንባር ቀደም ሚና መጫወቱን አስታውሷል። ይህም “ሁሉንም ዜጎች በእኩልነት የሚያገለግል ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓት እና አዲስ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት” እንዲፈጠር ማድረጉን ገልጿል።
ይሁን እንጂ ሕገ-መንግሥቱ በተደጋጋሚ እንደተጣሰ የጠቀሰው አስተዳደሩ፤ “በሕዝባችን ላይ ከተፈጸሙት ሊገለጹ የማይችሉ ግፎች እና የዘር ማጥፋት ድርጊቶች ባሻገር፣ አሁን ደግሞ ሕገ-መንግሥቱንም ሆነ የፕሪቶሪያውን ስምምነት በግልጽ የሚጻረር አዲስ ውሳኔ ተላልፏል” ብሏል። መግለጫው አክሎም፣ ውሳኔው “በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና የተሰጣቸውን የትግራይ ሕገ-መንግሥታዊ ድንበሮች በቀጥታ አደጋ ላይ የሚጥል ነው” ሲል ከሷል።
ጊዜያዊ አስተዳደሩ ይህንን ውሳኔ “በጽኑ እንደሚያወግዘው” ገልጾ፣ ውሳኔው “የትግራይ ሕዝብ ውክልና እና ድምፅ በሌለበት ምክር ቤት የጸደቀ” ነው ብሏል። ድርጊቱ “ከባድ እና ዘርፈ-ብዙ መዘዞች” እንደሚኖሩት ያስጠነቀቀው መግለጫው፣ መንግሥት “ይህን አደገኛ መንገድ በአስቸኳይ እንዲያጤነው እና ውሳኔውን እንዲያስተካክል” ጠይቋል።
ይህ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ጠንከር ያለ ምላሽ የመጣው፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አምስት የምርጫ ክልሎች (ሁመራ፣ አዲረመጽ፣ ፀለምቲ፣ ኮረም ኦፍላ እና ራያ አላማጣ) የይገባኛል ጥያቄያቸው እልባት እስኪያገኝ ድረስ ከትግራይ ክልላዊ መንግሥት ውጭ በሆነ መንገድ ምርጫ እንዲያካሂዱ ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ትዕዛዝ ማስተላለፉን ተከትሎ ነው።
የፌዴሬሽን ምክር ቤት ይህን ውሳኔ ያስታወቀው ቦርዱ ቀደም ሲል የምርጫ ከልሎችና ጣቢያዎች ዝርዝር ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ጥር 25 ቀን 2018 ዓ.ም. ለቦርዱ በጻፈው ደብዳቤ ነው።
ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዛሬ ባወጣው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት በትግራይ እና በአማራ ክልሎች መካከል የይገባኛል ጥያቄው ያለባቸው “አከራካሪ” አምስት የምርጫ ክልሎች ጉዳይ በሕገ-መንግሥት ውሣኔ ሲፈታ አመቺ ጊዜ ተመርጦ ምርጫው ወደፊት እንዲካሄድ ወስኗል።አስ
