በ2012 ዓ.ም ተጀምሮ በአዲስ አበባ ከተማ አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው የኢትዮጵያ ብሔራዊ የንግድ ፖርታል የማስፋፊያ ፕሮጀክቱን በሶስት የክልል ከተሞች ማለትም በ አዳማ፣ ባሕርዳር እና ድሬዳዋ በማድረግ በዛሬው ዕለት ተመርቋል።
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የማስፋፍያ ፕሮጀክቱን ያደረገው ከአውሮፓ ህብረት ጋር በመተባበር መሆኑን ተጠቁሟል።
በምርቃት መርሐግብሩ ላይ ንግግር ያደረጉት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ ዶ/ር በለጠ ሞላ እንደገለጹት የማስፋፊያ ፕሮጀክቱ መጠናቀቅ የኢትዮጵያ መንግስት ውጤታማ እና ቀልጣፋ አገልግሎቶችን ለማቅረብ ያለውን ቁርጠኝነት ያሳያል ብለዋል።
አክለውም የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ጋር በተጣጣመ መልኩ፣ የኢትዮጵያን ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ለውጥ ለማፋጠን ፈጠራ ያላቸውን እና ተለዋዋጭ የኤሌክትሮኒክስ አገልግሎቶችን፣ የኤሌክትሮኒክስ አስተዳደርን እና የዲጂታል ስራዎች የማስፋፋት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።
ፕሮጀክቱ የአዳማ፣ የባህር ዳር እና የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮችን ያካተተ ሲሆን ይህም በዋናነት የግንባታ ፈቃድ አሰጣጥን ጨምሮ የመንግስት አገልግሎቶችን በዲጂታል ሲስተም ለማቅረብ ያስችላቸዋል ተብሏል።
ማስፋፊያው በተጨማሪም ደንበኞች የሚፈልጓቸውን የአገልግሎት ክፍያዎች በኦንላይን መክፈል የሚችሉበትን አዲስ ስርዓት መዘርጋቱ ተመላክቷል።
