የሚኒስትሮች ምክር ቤት የካቲት 23 ቀን 2018 ዓ.ም. ያፀደቀው አዲሱ የቱሪዝም ፖሊሲ፣ የዘርፉን የአገር ውስጥ ጥቅል ምርት (GDP) ድርሻ ከ3 በመቶ ወደ 10 በመቶ ለማሳደግ ማለሙን የቱሪዝም ሚኒስቴር አስታወቀ።
የቱሪዝም ሚኒስትር ደኤታ አቶ ስለሺ ግርማ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ከ17 ዓመታት በኋላ የተሻሻለው ይህ ፖሊሲ ቀደም ሲል ትኩረት ያልተሰጣቸውን የአገር ውስጥ ቱሪዝም እንዲሁም የኮንፈረንስና ኤግዚቢሽን ዘርፎችን በልዩ ሁኔታ የሚያካትት ነው።
በተለይም እያደገ የመጣውን የኮንፈረንስ ቱሪዝም በሕግና በሥርዓት ለመምራት የሚያስችል ራሱን የቻለ ተቋም ለማቋቋም ፖሊሲው መንገድ የሚከፍት ሲሆን፣ ይህም ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ ታቅዶ የተዘጋጀ ነው።
ፖሊሲው ሚኒስቴሩ ለዘርፉ ልማት የሚያስፈልጉ የሕግ ማዕቀፎችንና ስትራቴጂዎችን ለመንደፍ የነበረበትን የመሠረታዊ ሰነድ እጥረት እንደሚፈታውም ተገልጿል።
