የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ እስማኢል ባጋሃይ፤ ሀገራቸው በቱርክ፣ በቆጵሮስ እና በአዘርባጃን ላይ ጥቃት ፈጽማለች ተብሎ የሚናፈሰውን መረጃ አስተባበሉ።
ባለፈው ሳምንት ተፈጽመዋል የተባሉትን ጥቃቶች አስመልክተው በሰጡት መግለጫ፤ ከኢራን ግዛት የተሰነዘረ ምንም ዓይነት ጥቃት አለመኖሩን አረጋግጠዋል።
ቃል አቀባዩ አክለውም፤ ጥቃቶቹ በኢራን እና በጎረቤት ሀገራት መካከል ቅራኔ ለመፍጠር በ“ጠላት” የተደራጁ ሴራዎች ሊሆኑ እንደሚችሉ አስጠንቅቀዋል።
በአሁኑ ወቅት ስለ ተኩስ ማቆም ድርድር የሚነሱ ሃሳቦችን ውድቅ ያደረጉት ባጋሃይ፤ ወታደራዊ ግጭቶች ባልቆሙበት ሁኔታ ስለ ሸምግልና ማውራት “አስፈላጊ አይደለም” ብለዋል። “ይህ ጦርነት በእኛ ላይ የተጫነ እንጂ እኛ የጀመርነው አይደለም” ሲሉ የገለጹት ቃል አቀባዩ፤ በአሁኑ ወቅት የሀገሪቱ ቀዳሚ ትኩረት ሉዓላዊነትን ማስጠበቅ ላይ ብቻ መሆኑን አስገንዝበዋል።
