የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት አሰራር ለሙስና እና ብልሹ አሰራር ተጋላጭ እንደሆነ ጥናት አሳይቷል።
የፌደራል የሥነምግባር እና የፀረሙስና ኮሚሽን በ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት አሰራር ስርዓት ላይ ጥናት አድርጓል።
በኢንቨስትመንት አዋጁ እንዲሁም በኢንቨስትመንቶች ውስጥ ለሚሰሩ የውጭ አገር ሰራተኞች የስራ ፈቃድ የሚሰጥበት መመሪያ ከሚፈቅደዉ ዉጪ የስራ ፍቃድ እንደተሰጠ ጥናቱ ጠቁሟል።
ባለሀብቱ ለኢንቨስትመንቱ አስፈላጊ የሆኑ የዉጪ ሀገር ዜጎችን መቅጠር የሚችል ቢሆንም ከመቅጠሩ በፊት የስራ መደቡ በሚፈልገው ደረጃ ተመሳሳይ ሙያ ወይም ልምድ ያላቸው ኢትዮጵያውያን አለመኖራቸውን ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግ አዋጁ ገልፆል።
የኮምሽኑ ጥናት የአገር ውስጥ ባለሙያዎች እጥረት መኖሩ ሳይረጋገጥ የትምህርት ዝግጁታቸው ላልተገለጸ የውጭ ሠራተኞች የሥራ ፈቃድ መሰጠቱ ጠቁሟል።
የጥናቱ ግኝቶችን ለኢንቨስትመንት ኮምሽን ያቀረበዉ የሥነምግባር እና የፀረሙስና ኮሚሽን ሌሎች ለብልሹ አሰራር በር የከፈቱ ነጥቦችንም አንስቷል።
በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮምሽን የመረጃ ቋት ዉስጥ ለዓመታት ያለ ተግባር የቆዩ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ፈቃዳቸው ሳይሰረዝ በ”ኢንአክቲቭ” ምድብ ውሳኔ ሳይሰጥባቸው መቀመጥ ለብልሹ አሰራር አጋላጭ ማድረጉን ሰምተናል።
በሌላ በኩልም አንዳንድ ኢንቨስተሮች ያገለገሉ መሳሪያዎችን ቀለም በመቀባት እንደ አዲስ በማስመዝገብ ከቀረጥ ነፃ አገልግሎት እያገኙ መሆኑን ከጥናቱ ለማወቅ ተችሏል።
በዚህም የግብር እፎይታ ለማግኘት ሲባል ፕሮጀክቶችን ለማስተላለፍ መሞከራቸው የአሰራር ስርዓቱ ለብልሹ አሰራር የተጋለጠ ያደርገዋል ተብሏል።
በጥናቱ ምክረ ሀሳብ ላይም የግብር እፎይታ ያገኙ ባለሀብቶች በአግባቡ ስለመጠቀማቸው ግልጽ ቁጥጥር ማድረግ ይገባል ተብሏል።
በፌደራል የስነ ምግባር እና ፀረ ሙስና ኮምሽን የሙስና መከላከልና ጥናት ዘርፍ ም/ኮሚሽነር እሸቴ አስፋው እንደገለፁት በጥናቱ የተለዩ ግኝቶችንና ክፍተቶችን በፍጥነት መፍታት ያስፈልጋል ብለዋል።
