መካከሏ ገነት፤ ዳሯ እሳት ይሁን
መስከረም 21 ብዙሃን ማርያም ይባላል፡፡ ይህ ዕለት ስለ ሁለት ነገር ይዘከራል፡፡ የመጀመሪያው በ325 ዓ.ም በኒቂያ ጉባኤ 318ቱ ሊቃውንት አርዮስን አውግዘው የለዩበትና “በአንድ አምላክ እናምናለን” የሚለውን የሃይማኖት ጸሎትና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎችን ደንግገዋል፡፡
ኒቅያ ለዚህ ጉባኤ የተመረጠችበት ምክንያትም ጳጳሱን ከማኅበረ ካህናቱ፤ ንጉሡን ከሠራዊቱ ጋር አጠቃላ ለመያዝ የምትችል ሰፊና ምቹ ቦታ ከመሆኗ ባሻገር ለሁሉም አማካይ ሥፍራ ስለ ነበረች ነው፡፡
ሊቃውንቱ ጉባኤውን ያካሔዱት ኅዳር 9 ቀን ይኹን እንጂ በአንድነት የተሰባሰቡት መስከረም 21 ቀን ስለ ነበረ ይህች ዕለት “ብዙኃን ማርያም” እየተባለ ይጠራል፡፡
ብዙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ለሃይማኖታዊ ጉባኤ የተሳባሰቡበት ዕለት ነውና፡፡ አንድም መስከረም 21 ቀን የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በግሸን ደብረ ከርቤ የገባበትና በዓሉ የተከበረበት ዕለት ነው፡፡
አፄ ዳዊት በዘመናቸው በኢትዮጵያ ቸነፈር ተከሥቶ ሕዝቡ ስለ ተሰቃየባቸው እጅግ አዘኑ፤ በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ቢያመለክቱም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላኩ ባሕታዊ መጥተው “የጌታችንን መስቀል አስመጥተህ በአገርህ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አሠርተህ ብታስቀምጥ ረሃቡ፣ ቸነፈሩ ሁሉ ይታገሥልሃል” አሏቸው፡፡
ዐፄ ዳዊትም ከብዙ ገጸ በረከት ጋር “የጌታችንን መስቀል ላኩልኝ” የሚል መልእክት አስይዘው መልእክተኞችን ወደ ኢየሩሳሌም ሰደዱ፡፡ መልእክተኞቹም በታዘዙት መሠረት መስቀሉን ይዘው መምጣታቸውን ዐፄ ዳዊት ሲሰሙ “ክተት ሠራዊት ምታ ነጋሪት” ብለው መስቀሉን ለመቀበል ጉዞ ጀመሩ፡፡
ዐፄ ዳዊት ሱዳን ስናር ደርሰው ከመልእክተኞቹ ጋር ተገናኝተው መስቀሉን በክብር አጅበው ወደ መካከል ኢትዮጵያ ለማስገባት ሲነሡም ከበቅሏቸው ወድቀው ጥቅምት 9 ቀን ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡
ሠራዊታቸው ተደናግጠው የጌታችንን መስቀል እዚያው ትተው የዐፄ ዳዊትን አስከሬን ይዘው ተመለሱ፡፡ መስቀሉ በስናር ከቆየ በኋላ የዐፄ ዳዊት ልጅ ዘርዐ ያዕቆብ ሲነግሡ ወደ መሃል ኢትዮጵያ አምጥተው ቤተ ክርስቲያን አሠርተው ለማስቀመጥ ቢያስቡም ምቹ ቦታ ግን ሊያገኙ አልቻሉም፡፡
ንጉሡና ሠራዊታቸው ምቹ ቦታ ሲፈልጉ መስቀሉን በኤረር ተራራ፣ በደብረ ብርሃን፣ በመናገሻ ዓምባና በእንጦጦ ብዙ ጊዜ አስቀምጠውት ቆይተዋል፡፡ በኋላም እግዚአብሔር አምላክ “መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አኑር” የሚል ራእይ ገለጸላቸው፡፡
መስቀሉን ወደ ወሎ ሀገረ ስብከት እንዲወስዱትም አዘዛቸው፡፡ ንጉሡና ሠራዊታቸው በእግዚአብሔር መሪነት መስቀሉን ይዘው ወሎ ሲደርሱም ጌታችን የግሸን ተራራን እያመለከተ “መስቀሌን በመስቀለኛ ተራራ ላይ አኑር” ይላቸው ነበር፡፡
ንጉሡም መስቀሉን ይዘው ወደ ቦታው በማምራት ቤተ ክርስቲያን አሠርተው መስከረም 21 1446 ዓ.ም የጌታችንን መስቀል በክብር አስቀምጠውታል፡፡
ከዚህ በኋላ ንጉሡ “መካከሏ ገነት፤ ዳሯ እሳት ይሁን! የበረረ ወፍ፣ የሠገረ ቆቅ አይታደንባት! በድንገት ሰው የገደለ፣ ቋንጃ የቈረጠ ወንጀለኛ አይያዝባት!” ብለው ዐዋጅ ነግረዋል፡፡ የእመቤታችን ጽላትም አብሮ በግሸን ደብረ ከርቤ እንዲቀመጥ አድርገዋል፡፡
ስለዚህም መስከረም 21 ቀን በየዓመቱ በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል፡፡ ኀጢአታቸውን ለካህን ተናዘው፣ ንስሐ ገብተው በዚህ ዕለት ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ በመሔድ የሚጸልዩና የሚማጸኑ ምእመናን ሁሉ እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደሚያገኙም ጤፉት በተባለችው መጽሐፍ ተጠቅሷል፡፡ ገዳማውያኑም ይህን መሠረት አድርገው በቃል ኪዳኗ ይመጸኗታል፡፡ ገዳማቸውን እንደግፍ በዓታቸውን እናጽና፡፡
ድጋፍ ለማድረግ:- ሙትአንሳ ማር ቅዱሰ ሚካኤል አንድነት ገዳም
ኢትዮጲያ ንግድ ባንክ
1000442598391 ወይም አቢሲኒያ ባንክ 141029444
የገዳሙ ስልክ ቁጥር:-0918077957 ወይም 0938644444
