የደቡብ ሱዳን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት ሪክ ማቻር (ዶር) በጁባ ከተማ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የፓርቲያቸው የውጭ ግንኙነት ኮሚቴ ሊቀመንበር በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል።
የፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር የረጅም ጊዜ ተፎካካሪ የሆኑት ማቻር “20 ከባድ የጦር መሳሪያ የታጠቁ ተሽከርካሪዎች” በተሳተፉበት ኦፕሬሽን ከቤታቸው ተወስደዋል ሲል ፓርቲያቸው ኤስፒኤልኤም-አይኦ (SPLM-IO) አስታውቋል።
ፓርቲው የፀጥታ ኃላፊዎች “ኢ-ሕገመንግስታዊ ድርጊት” ፈጸመዋል ሲል ድርጊቱን አውግዟል። በተጨማሪም ሪክ ማቻር በቁጥጥር ስር የዋሉበት ምክንያት “ግልፅ አለመሆኑንም” ገልጿል።
በደቡብ ሱዳን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ተልዕኮ እስሩ ሀገሪቷን ወደ አዲስ ግጭት እንዳያስገባ አስጠንቅቋል። የድርጅቱ ኃላፊ ኒኮላስ ሃይሶም መሪዎቹ ወደ ሰፊ ግጭት መመለስን ለማስወገድ ራሳቸውን መቆጣጠር እንዳለባቸው አሳስበዋል።
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት እንደገለጸው፤ ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ ለኪር እና ለማቻር ታማኝ በሆኑ ኃይሎች መካከል ግጭት ተከስቷል። የተፈጠረው ውጥረትም እያየለ ባለበት ወቅት #ኖርዌይ እና #ጀርመን ኤምባሲዎቻቸውን ለጊዜው ዘግተዋል።
ካለፈው ወር ጀምሮ ወደ 50,000 የሚጠጉ ሰዎች ከእላኛው ናይል አካባቢ መፈናቀላቸውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አስታውቋል ሲል የጀርመን ድምጽ ዘግቧል።
