የደቡብ ሱዳን መንግሥት ግብፅ እና ሱዳን የዓባይ ተፋሰስ አገራት የትብብር ማዕቀፍ ስምምነትን እንዲፈርሙና ፍትሐዊ የውኃ አጠቃቀም ሥርዓት እንዲሰፍን ጥሪ አቀረበ።
ጥሪው የቀረበው ትላንት እሁድ በጁባ በተከበረው የ”ዓባይ ቀን” በዓል ላይ ሲሆን፣ የደቡብ ሱዳን የውኃ ሀብትና መስኖ ሚኒስትር ጄምስ ማዊች ማኩዋች ግብፅ፣ ሱዳን፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና ኬንያ ስምምነቱን በመቀላቀል ቀጣይነት ያለው የውኃ አስተዳደር እንዲሰፍን በጋራ እንዲሠሩ አሳስበዋል።
እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በጥቅምት 13 ቀን 2024 በይፋ ሥራ ላይ የዋለው ይህ የማዕቀፍ ስምምነት፣ እስካሁን በኢትዮጵያ፣ ሩዋንዳ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ኡጋንዳ፣ ታንዛኒያ እና ቡሩንዲ መጽደቁ ይታወሳል።
ስምምነቱ የዓባይ ተፋሰስ አገራት በግዛታቸው ውስጥ ያለውን የውኃ ሀብት “በፍትሐዊና ምክንያታዊ በሆነ መንገድ” የመጠቀም መብት እንዳላቸው ይደነግጋል። ሆኖም ግብፅና ሱዳን “ስምምነቱ ከቅኝ ግዛት ዘመን ስምምነቶች ያገኘነውን ታሪካዊ መብት ይጋፋል” በሚል እስካሁን ለመፈረም ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቆይተዋል።
