ዶይቸ ቨለ፣ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኀን ባለሥልጣን ቦን ከተማ የሚገኙትን የአማርኛው ሬዲዮ ጣቢያ ጋዜጠኞችን ጭምር በደፈናው ወንጅሏል ሲል አዲስ ባወጣው መግለጫ ተቃውሞውን ገለጸ።
ባለሥልጣኑ፣ በቦን የሚገኙ ሠራተኞቹ ላይ “የተሳሳተ” እና “ሁከት” ሊቀሰቅስ ወይም “ሰላም” እና “ጸጥታ” ሊያናጋ የሚችል መረጃ ያሰራጫሉ የሚል ክስ ማቅረቡን ጣቢያው አመልክቷል።
የአማራ እና ትግራይ ክልሎች ዘጋቢዎቹ በዘላቂነት መታገዳቸውን የተቃወመው ጣቢያው፣ ባለሥልጣኑ ለእገዳው “ተጨባጭ ምክንያት” አላቀረበም በማለት ወቅሷል። ዶይቸ ቨለ የባለሥልጣኑን ክሶች ውድቅ በማድረግ ከዘጋቢዎቹና ቦን ከሚገኙ ሠራተኞቹ ጎን እንደሚቆም አስታውቋል።
