የዓለም ጤና ድርጅት የካንሰር በሽታ ስርጭት በዓለም ዙሪያ እየጨመረ መምጣቱን በሪፖርቱ አመላክቷል። በቀጣዮቹ ዓመታት 92 በመቶ የሚሆነው የዓለም ህዝብ በበሽታው የመጠቃት ወይም በቅርብ ቤተሰቡ በኩል በተዘዋዋሪ ተፅዕኖው እንደሚደርስበት ነው የገለጸው።
በጤና አገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚታየው ከፍተኛ የኢ-ፍትሐዊነት ክፍተት ምክንያት በየጊዜው የሚታየው የበሽታው ተጽዕኖ እየተባባሰ መምጣቱንም አንስቷል።
የካንሰር ህመምተኞች ቁጥር መጨመር በዋናነት ከአኗኗር ዘይቤ ለውጥ፤ ከብክለት መጨመር እና የህዝብ ቁጥር እድገት ጋር በተያያዙ ምክንያቶች እንደሆነ አመልክቷል።
ይሁን እንጂ በዝቅተኛ እና መካከለኛ ገቢ ባላቸው ሀገራት የቅድመ ምርመራ እና የህክምና አገልግሎት ተደራሽነት ውስን መሆን፣ ለበሽታው ተጎጂዎች የሞት ምጣኔ መጨመር ዋናው ምክንያት እንደሆነ ተጠቅሷል።
በ2024 ብቻ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከ20.6 ሚሊዮን በላይ ሰዎች በካንሰር መያዛቸው ተረጋግጧል። በዚሁ ዓመት 9.7 ሚሊዮን ሰዎች በበሽታው ህይወታቸው አልፏል።
የካንሰር ታማሚዎች ቁጥር በ2050 ወደ 35 የ66.7 በመቶ ጭማሪ ያሳያል ቢባልም ዝቅተኛ ገቢ ባላቸው ሀገራት ግን ሥርጭቱ እስከ 133 በመቶ ሊያድግ እንደሚችል ተገምቷል።
የሳንባ ካንሰር በ1.86 ሚሊዮን ሰዎች ህልፈት አንደኛውን ደረጃ ይዟል። በመቀጠል የአንጀት ካንሰር የአንጀት ካንሰር ወይም የፊንጢጣ ካንሰር 918,000፣ የጉበት ካንሰር 732,000፣ የጡት ካንሰር 694,000 እና የጨጓራ ካንሰር 642,000 ሰዎችን ህይወት በመቅጠፍ በቅደም ተከተል ተቀምጠዋል።
የዓለም ጤና ድርጅት፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚከሰቱት የካንሰር ህመሞች ውስጥ ወደ 40 በመቶ የሚጠጉት በቅድመ መከላከል ሊወገዱ የሚችሉ ስለመሆናቸው ይገልጻል።
@TikvahethMagazine
