በጃፓን ቶኪዮ እየተካሄደ በሚገኘው 20ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የሴቶች 5 ሺህ ሜትር የፍጻሜ ውድድር ዛሬ ይደረጋል፡፡
ቀደም ባሉት ዓመታት ኢትዮጵያ በርካታ ድሎችን በተቀዳጀችበት የሴቶች 5ሺህ ሜትር ውድድር ዛሬስ ምን አይነት ውጤት ታስመዘግብ ይሆን የሚለው ይጠበቃል፡፡
ኢትዮጵያ ተጨማሪ ሜዳልያዎችን ታገኝበታለች ተብሎ በሚጠበቀው የዛሬው የፍጻሜ ውድድር በአትሌት ጉዳፍ ፀጋይ፣ መዲና ኢሳ እና ፋንታዬ በላይነህ ትወከላለች፡፡
በዚህ ርቀት ኢትዮጵያ በብርቅዬ አትሌቶቿ ስሟ በዓለም አዳባባይ ከፍ ብሎ መጠራቱ የሚታወስ ሲሆን፥ በተለይም በፈረንጆቹ 2005 በሄልሲንኪ በተካሄደው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከ1ኛ እስከ 4ኛ ያለውን ደረጃ በመያዝ ማጠናቀቃቸው አይዘነጋም፡፡
በወቅቱ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ይህንን ታሪክ ሲሰሩ የአንድ ሀገር አትሌቶች ከ1 እስከ 4ኛ ያለውን ደረጃ ይዞ በማጠናቀቅ በሻምፒዮናው ታሪክ ቀዳሚ መሆናቸው ይታወሳል፡፡
አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ በቀዳሚነት ስታጠናቅቅ መሰረት ደፋር፣ እጅጋየሁ ዲባባ እና መሰለች መልካሙ ከ2 እስከ 4 ተከታትለው በመግባት ይህን የማይደገም የሚመስል ሰርተዋል፡፡
ኢትዮጵያ ከዓመታት በፊት በዚህ ርቀት ስኬታማ ብትሆንም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን በሚደረጉ ውድድሮች በሜዳልያ ሰንጠረዥ ውስጥ ለመግባት እየተቸገረች ትገኛለች፡፡
በፈረንጆቹ 2023 በሀንጋሪ ቡዳፔስት በተደረገው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በሴቶች 5ሺህ ሜትር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በኬንያውያን የበላይነት ተወስዶባቸው ከሜዳልያ ሰንጠረዥ ውጪ መሆናቸው ይታወሳል፡፡
ዛሬ በሚካሄደው የሴቶች 5ሺህ ሜትር የፍጻሜ ውድድር ኢትየጵያውያን አትሌቶች የተወሰደባቸውን የበላይነት ያስመልሱ ይሆን የሚለው ተጠባቂ ነው፡፡
በማጣሪያው ውድድር በተመሳሳይ ምድብ ውስጥ የነበሩት አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ 1ኛ እንዲሁም መዲና ኢሳ 5ኛ በመሆን ለፍጻሜ ሲያልፉ፥ በሌላኛው ምድብ የነበረችው አትሌት ፋንታዬ በላይነህ 6ኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቀቅ ነው ለዛሬው ፍጻሜ የበቃችው፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በርቀቱ የጠፋውን ድል ለመመለስ ብርቱ ፉክክር እንደሚያደርጉ የሚጠበቁበት የፍጻሜ ውድድር ዛሬ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ29 ይጀምራል፡፡
ኢትዮጵያ እስካሁን በጃፓን ቶኪዮ እየተካሄደ ባለው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሁለት የብር እና ሁለት የነሃስ በድምሩ አራት ሜዳልያ አግኝታለች፡፡
ኤፍ ኤም ሲ
