በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የግል የኢንቨስትመንት ባንክ የሆነው ወጋገን ካፒታል ኢንቨስትመንት ባንክ የ2017 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸሙን ይፋ አድርጓል።
የኢንቨስትመንት ባንኩ 7.9 ሚሊዮን ብር ገቢ ያስመዘገበ ቢሆንም፣በመሠረተ-ልማት ግንባታ ላይ በዋለ ስትራቴጂካዊ ኢንቨስትመንት ሳቢያ፣ ወጪው 22.4 ሚሊዮን ብር መድረሱን አስታውቋል።
የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ወ/ሮ ብሩታዊት ዳዊት፣ የፋይናንስ ውጤቱ በመክፈቻ ምዕራፍ የሚጠበቅ ነው ብለዋል።
ትኩረታቸው ፈጣን ትርፍ ላይ ሳይሆን፣ በቋሚ ንብረቶች፣ በሠራተኞች ሥልጠናና ልምድ ባላቸው የውጭ ባለሙያዎች ቅጥር ላይ በመዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ “ለዘላቂ እድገት ጠንካራ መሠረት መጣል” ላይ እንደነበር አስረድተዋል። ባንኩ በቀጣዩ የሒሳብ ዓመት ትርፋማ ይሆናል የሚል እምነት እንዳላቸውም ገልጸዋል።
እኤአ በመጋቢት 2025 ዓ.ም. ሥራውን የጀመረው ወጋገን ካፒታል ኢንቨስትመንት ባንክ በአገሪቱ አዲስ በተቋቋመው የፋይናንስ ዘርፍ ወሳኝ ተዋናይ እንደሚሆን ወ/ሮ ብሩታዊት አክለዉ ተናግረዋል።
ከተጀመረ ከሁለት ወራት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ፣ ባንኩ ከባንክ፣ ኢንሹራንስ እና ሪል እስቴት ጨምሮ ከተለያዩ ዘርፎች 15 ደንበኞችን በመሳብ፣ ስድስት የአማካሪነትና የደላላነት ኮንትራቶችን የፈረመ ሲሆን፣ 37 የኢንቨስትመንት አካውንቶችንም መክፈቱን ካፒታል ሰምቷል።
ባንኩ የጀመረው በ385 ሚሊዮን ብር የተከፈለ ካፒታል ሲሆን፣ ጠቅላላ ንብረቱ 387.8 ሚሊዮን ብር እንዲሁም የባለቤትነት ድርሻው 374.8 ሚሊዮን ብር መድረሱን ዓመታዊ ሪፖርቱ ያሳያል።
CapitalNews
