ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ላይ ባደረጉት ንግግር ትስስር እና የባሕር ተደራሽነት ለኢትዮጵያ ዘላቂ ልማት ያለው ጠቀሜታ ወሳኝ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ በአቪዬሽንና በዲጂታል መሠረተ ልማት ዘርፍ ከፍተኛ ስራን እየሰራች መሆኑን ገልጸዋል ፡፡
“በኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰዎችን እናገናኛለን፣ ገበያዎችን እናስተሳስራለን እንዲሁም ሸቀጦችን እናንቀሳቅሳለን፤ ይህንንም ፍጥነት ለማስቀጠልም አኅጉራችንን በዓለም አቀፍ የእሴት ሰንሰለት ማዕከል የሚያደርጋትን የቀጣይ ትውልድ መግቢያ በር የሆነ በአፍሪካ ትልቁን አየር ማረፊያ እየገነባን ነው” ብለዋል።
ከ130 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ላላት ኢትዮጵያ የረዥም ጊዜ ብልጽግና የተለያዩ የመዳረሻ መንገዶችን እንደሚፈልግ አፅንኦት ሰጥተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የኢትዮ ቴሌኮም በመላው አፍሪካ መስፋፋት ዲጂታል መከፋፈል አሻጋሪ ድልድይ ለመሆን እና አኅጉራዊ ውህደትን ለማጠናከር የሚደረገው ጥረት አንዱ አካል መሆኑን አንስተዋል።
