አትሌት ትዕግስት አሰፋ ዓለም አቀፍ የድንቃ ድንቅ መዝገብ እውቅና ተሰጣት
በትናንትናው ዕለት ለ45ኛ ጊዜ በተካሄደው የለንደን ማራቶን ክብረ ወሰን በመስበር ያሸነፈችው አትሌት ትዕግስት አሰፋ፤ ከዓለም አቀፉ የድንቃድንቅ መዝገብ (World Guinness Book of Record) እውቅና ተሰጥቷታል።
በፖሪሱ ኦሎምፒክ በሲፋን ሀሰን ተቀድማ የብር ሜዳሊያ ያገኘችው አትሌት ትዕግስት፤ በትናንትናው የለንደን ማራቶን በቀዳሚነት በመግባት አሸንፋለች፡፡ ኬንያዊቷ ጆክሊን ጂኮስካ ሁለተኛ እንዲሁም ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ የኔዘርላንድ አትሌት ሲፋን ሀሰን ሦስተኛ በመውጣት ውድድሩን አጠናቀዋል።
የሁለት ጊዜ የበርሊን ማራቶን አሸናፊዋ አትሌት ትዕግስት ውድድሩን ከ35ኛው ኪሎ ሜትር በኋላ ለብቻዋ ተነጥላ በመውጣት ያሸነፈች ሲሆን፤ ይህም ድል 3ኛ የሜጀር ማራቶን ድሏ ሆኖ ተመዝግቦላታል፡፡
በዚህም አትሌት ትዕግስት በሴት አሯሯጮች ብቻ በተካሄደውና በዓለም አትሌቲክስ የፕላቲኒየም ደረጃ በተሰጠው ማራቶን ላይ፤ 2 ሰዓት 15 ደቂቃ 50 ሰከንድ በመግባት አዲስ ክብረ ወሰን መስመዝገብ ችላለች፡፡
ይህም ሰዓቷ በሴቶች ብቻ የተሮጠ የዓለም ክብረወሰን “Women’s-only World Record” ተብሎ በዓለም ሪከርድነት ተመዝግቦላታል፡፡
ባለፈው ዓመት በዚሁ የለንደን ማራቶን ላይ በሴት አሯሯጮች ብቻ በተካሄደ ውድድር ኬንያዊቷ ፔሬስ ጄፕቺሪር 2 ሰዓት 16 ደቂቃ ከ16 ሰከንድ በመግባት የዓለምን ሪከርድ ይዛ የነበረ ሲሆን፤ አትሌት ትዕግስት ይሄን ሪከርድ በትናንትናው ዕለት በማሻሻሏ ነው ዕውቅናው የተሰጣት፡፡
በተጨማሪም አሸናፊዋ ኢትዮጵያዊቷ አትሌት ትዕግሥት አሰፋ ውድድሩን በቀዳሚነት በማጠናቀቋ 55 ሺሕ ዶላር አሸናፊ ሆናለች።
