የሊበራል ፓርቲ መሪው ማርክ ካርኔይ በካናዳ እየተካሄደ የሚገኘውን የፌደራል ምርጫ እንዳሸነፉ አስታውቀዋል፡፡
ምርጫውን ያሸነፉት ማርክ ካርኔይ ባስተላለፉት የድል መልዕክት፤ የአሜሪካው ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ በካናዳ ላይ የከፈቱትን “የንግድ ጦርነት” ለመመከት እንደሚሰሩ ቃል ገብተዋል፡፡
በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ማርክ ካርኔይ ከትራምፕ አስተዳደር የመጣውን፤ “ካናዳን ወደ አሜሪካ እንጣቃልላለን” የሚል እንቅስቀሴ አጥብቀው እንደሚዋጉ አስታውቀዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ የካናዳን ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ ቃል የገቡ ሲሆን፤ “አሜሪካ መሬታችንን፣ ውሃችንን እና የተፈጥሮ ሀብታችንን ትፈልጋለች” ሲሉም ተናግረዋል፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘም አዲሱ የካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር “ትራምፕ በፍፁም እኛን አይሰብሩንም” ሲሉ መልዕክት ማስተላለፋውን አልጀዚራ ዘግቧል፡፡
የአሜሪካ ፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ ካናዳን የአሜሪካ 51ኛ ግዛት ለማድረግ ያላቸውን እቅድና የወቅቱን የሀገሪቱን ጠቅላይ ሚኒስትር ጀስቲን ትሩዶንም የግዛቷ አስተዳዳሪ ሊያደርጉ እንደሚችሉ ከገለጹ በኋላ፤ ግንኙነታቸው መሻከሩ ይታወቃል፡፡
ማርክ ካርኔይ ምንም እንኳን የጠቅላይ ሚኒስትር ጀስቲን ትሩዶን ስልጣን መልቀቅን ተከትሎ ባለፈው ወር ወደ ኃላፊነት የመጡ ቢሆንም፤ በተደረገው ምርጫ ማሸነፋቸው ትሩዶ በትራምፕ ላይ ያላቸውን ጠንካራ አቋም ያስቀጥላሉ ተብሎ እምነት ተጥሎባቸዋል፡፡
በዚህም የሊበራል ፓርቲው ማርክ ካርኔይ የተቃዋሚውን ኮንዘርቫቲቭ ፓርቲ ተወካይን ያሸነፉ ሲሆን፤ ይህም የሊበራል ፓርቲን ለአራት ተከታታይ ዙር ሀገሪቱን እንዲመራ አስችሎታል ተብሏል፡፡
ካርኔይ ለጠቅላይ ሚኒስትርነት መመረጣቸውን ተከትሎም ከተለያዩ የዓለም ሀገራት “የእንኳን ደስ አለዎ!” መልዕክት እየተላከላቸው ሲሆን፤ የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ኬይር ስታርመር በፀጥታ፣ በንግድና በሌሎች ዓለማቀፍ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመስራት ያላቸውን ፍልጎት ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ የቻይና መንግሥት ቃል አቀባይ ጎ ጃይኩን የቻይና-ካናዳን የሁለትዮሽ ግንኙነት “በእኩልነትና በጋራ መከባበር አጠናክሮ ለማስቀጠል” ቻይና ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላት ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የአውሮፓ ሕብረት ፕሬዝዳንት አንቶኒዮ ኮስታ “የእንኳን ድስ አለዎት” መልዕክት ካስተላለፉ በኋላ፤ “እኛ ተመሳሳይ እሴቶችንና የተባበሩት መንግሥታት ቻርተሮችን እንጋራለን” ብለዋል፡፡
ኮስታ አክለውም “እኛ ሕግ-መር ዓለም አቀፍ ስርዓትን እንከተላለን” ሲሉም፤ ቻይና “በጋራ መከባበር መርህ ላይ በጋራ እንሰራለን” ስትል ከላከችው መልዕክት ጋር የሚቀራረብ ሃሳብ አጋርተዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም አውሮፓሕህብረት ኮሚሽን ፕሬዝደንት ኡርሱላ ቮን ዴር ሌየን ለጠቅላይ ሚኒስትር ካርኔይ በላኩት “የእንኳን ደስ አለዎት!” መልዕክት “በአውሮፓና በካናዳ መካከል ያለው ትስስር ጠንካራ ነው፤ የበለጠ እየጠነከረ ነውም” ብለዋል፡፡
ፕሬዝዳንቷ አክለውም፤ “የጋራ ዲሞክራሲያዊ እሴቶቻችንን እንጠብቃለን፤ ባለብዙ ወገንነትን እና ነፃና ፍትሃዊ የንግድ ውድድርን እናሳድጋለን” ሲሉ ለአዲሱ የካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር መልዕክታቸውን ልከዋል፡፡
