የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ፤ ተማሪዎች ያላቸውን ድግሪ ተጠቅመው ያለምንም ሌላ መመዘኛ የውጭ ሀገር ስራ እንዲያገኙ ለማድረግ ዕውቅና ማግኘቱን አስታወቀ።
የዩኒቨርስቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ደረጃ እንግዳ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤ ዩኒቨርሲቲው በአፕላይድ ሳይንስ የትምህርት ዘርፍ ማለትም በባይዮ ቴክኖሎጂ፣ በምግብ ሳይንስና በአመጋገብ ስርዓት፤ በኬሚካል ኢንዱስትሪና በጂኦሎጂ ዓለም አቀፍ ዕውቅና አግኝቷል።
ዩኒቨርሲቲው ያገኘው ዕውቅና በተለያዩ መርሃግብሮች የተመረቁ ተማሪዎች ያለምንምን መመዘኛ በውጭ ሀገራት ስራ እንዲያገኙ ያደርጋል ብለዋል።
ተማሪዎች የተመረቁበትን ድግሪ ይዘው በውጭ ሀገር ስራ መቀጠር አይችሉም ነበር፤ ከዚህ በፊት በሚቀጠሩበት ሀገር መመዘኛ መፈተን ግዴታ ነበር፤ አሁን የተገኘው ዕውቅና በድግሪያቸው ቀጥታ ስራ እንዲቀጠሩ የሚያደርግ ነው ሲሉ አብራርተዋል።
የተማሪዎቻችን ድግሪ ዓለም አቀፍ ዕውቅናን ያገኘ ባለመሆኑ የውጭ ሀገር ኢንዱስትሪዎች ወደ ሀገር ውሰጥ ሲገቡ የራሳቸውን የተማረ የሰው ሀይል ይዘው ነው የሚመጡት፤ ዕውቅናው ይህንን ችግር ይፈታል ሲሉ ገልጸዋል።
ዕውቅናው እ.ኤ.አ በ2023 ዓ.ም የተመረቁትንም እንዳሚያጠቃልል ተጠቁሟል፡፡
