የምሽት የግንባታ ፍቃድ አገልግሎት መኖሩን ባለማወቅ ምሽት ላይ ያለፍቃድ ግንባታ የመገንባት ከፍተኛ ዝንባሌ እየታየ ነዉ ተብሏል።
ሆኖም ምሽት ላይ የሚደረግ የግንባታ እንቅስቃሴ ፍቃድ የሚያስፈልገዉ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የግንባታ ፍቃድ እና ቁጥጥር ባለስልጣን ተናግሯል።
የግንባታ ፍቃድ እና ቁጥጥር ባለስልጣን ባለሙያ አቶ ሳሙኤል ደምሴ፤ ምሽት ላይ ግንባታ በመገንባት ሂደት አደጋዎች እየገጠሙ እንደሆነ ገልፀዋል።
ምሽት ላይ ለሚደረጉ ማንኛዉም የግንባታ አይነቶች በቅድሚያ ከሚመለከተዉ ተቋም ፍቃድ ማዉጣት ግዴታ ነዉ ብለዋል።
የዚህን የምሽት የግንባታ ፍቃድ አገልግሎት በቅድሚያ መዉሰድ እና መገንባት ላይ በአልሚዎች በኩል የግንዛቤ ክፍተት መኖሩንም ጠቁመዋል።
በመሆኑም ምሽት ላይ ለሚካሄድ ግንባታ በቅድሚያ ‹‹የምሽት ግንባታ ፍቃድ አገልግሎት››የሚል ፍቃድ መወሰድ ግዴታ እንደሆነ ተገልጿል።
አቶ ሳሙኤል “ያለ በቂ የግንባታ ግብዓት የሳይት ግንባታ መጀመር እና የሰራተኞች እና የስራ ላይ ደህንነት ሳይሟላ ከአዋጁ ጋር የሚጋጩ ለዉጦችን በቸልታ ማለፍ በተደጋጋሚ የሚታዩ ችግሮች ናቸዉ” ይላሉ፡፡
ባለሙያዉ ከዚህ ጋር በተያያዘ ከ2015 እስከ 2017 ባለዉ ሁለት ዓመት ጊዜ ዉስጥ በኮንስትራክሽን ስራዎች ላይ 1መቶ 42 የሞት አደጋ ማጋጠሙን ገልጸዋል፡፡
የህንፃ ግንባታ አማካሪዎች የሚያማክሩት ሳይት ያለበትን አደጋ አጋላጭ ሁኔታ በዝምታ የማለፍ ቸልተኝነት ይስተዋላል ብለዋል፡፡
ይሄን ችግር ለመፍታት እና አደጋዎችን ለመቀነስ የግንባታ ፍቃድ እና ቁጥጥር ባለስልጣን በተከታታይ ሙያዉ ላይ ለሚሳተፉ 10 ሺህ ሰዎች ስልጠና ለመስጠት ዕቅድ መያዙን ተናግረዋል።
በ2018 ዓ.ም ተከታታይነት ያለዉ የግንባታ ስራ የደህንነት ስልጠና ለመስጠት የግንባታ ፍቃድ እና ቁጥጥር ባለስልጣን ዝግጁ ሆኗል ሲሉ አቶ ሳሙኤል ደምሴ ነግረዉናል፡፡
