በአዲስ አበባ ጉብኝት እያደረጉ ያሉት የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭ፣ አፍሪካ ለምትከተለው የመፍትሔ መርህ ድጋፋቸውን ገልጸዋል። ሚኒስትሩ በአፍሪካ ያሉ ግጭቶችን ለመፍታት አህጉሪቱ በራሷ አቅም መምራት እንዳለባት አስታውቀዋል።
ይህንን የገለጹት ከአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ማሃሙድ አሊ ዩሱፍ ጋር ምክክር ካካሄዱ በኋላ ነው።
ሩሲያ በሰሃራ-ሳህል ቀጠና እና በአፍሪካ ቀንድ የሚስተዋሉ ቀውሶችን በልዩ ትኩረት እንደምትከታተል ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
በሱዳን፣ በደቡብ ሱዳንና በሊቢያ ያሉ አለመረጋጋቶች የሩሲያም አሳሳቢ አጀንዳዎች መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
አፍሪካ የምትገጥማቸውን ፈተናዎች ለመፍታት የምታደርገውን ጥረት ሩሲያ እንደምትደግፍም ተናግረዋል።
“የአፍሪካ ችግሮች በአፍሪካውያን መፍትሔ” የሚለውን መርህ ሩሲያ በጽኑ እንደምትከተል ላቭሮቭ አስገንዝበዋል።
ሩሲያ አፍሪካን የምታግዘው ይህንን መርህ ባከበረ መልኩ ብቻ መሆኑን አክለዋል። ጉብኝቱ ሩሲያ ከአፍሪካ ሕብረት ጋር ያላትን ስትራቴጂካዊ ግንኙነት ለማጠናከር ያለመ ነው ተብሏል።
