የኢትዮጵያ ጤና ሚኒስቴር ታኅሣሥ 3 ቀን 2018 ዓ/ም አንድ ተጨማሪ የማርበርግ ቫይረስ በሽታ ተጠቂ መመዝገቡን አስታወቀ።
ይህ አዲስ የተመዘገበው የቫይረሱ ተጠቂ ፣ ከህዳር 23 ቀን 2018 ዓ.ም. ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲሆን፣ ተጠቂው በጂንካ አጠቅላይ ሆስፒታል የህክምና ክትትል እየተደረገለት እንደሚግኝ ተገልጿል።
ይህ የቅርብ ጊዜ መረጃ፣ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጂንካ ከተማ ቫይረሱ መታየቱ ከታወቀበት ጊዜ ወዲህ የተረጋገጡትን አጠቃላይ የማርበርግ ተጠቂዎች ቁጥር ወደ 14 ከፍ አድርጎታል።
ከሚኒስቴሩ በተገኙ ሪፖርቶች መሠረት፣ እስካሁን በአጠቃላይ 1 ሺህ 765 የላቦራቶሪ ምርመራዎች ተካሂደው 14 ሰዎች ላይ ቫይረሱ የተገኘ ሲሆን፣ ከተረጋገጡት ተጠቂዎች መካከል ደግሞ ስምንት ሰዎች ሞተው አራት ሰዎች ከቫይረሱ ማገገም ችለዋል።
በአሁኑ ወቅትም ሁለት ታካሚዎች በቫይረሱ ተይዘው ሕክምና እየተደረገላቸው እንደ ሚገኝ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አስታውቋል።
የማርበርግ ቫይረስ በሽታ በአደገኝነቱ ከኢቦላ ጋር ተመሳሳይ ሲሆን፣ በሰውነት ውስጥ ከፍተኛ የደም መፍሰስና ሞትን ሊያስከትል የሚችል ገዳይ በሽታ ነው። የጤና ሚኒስቴር አዲስ የተመዘገበውን ጉዳይ ተከትሎ፣ የክትትልና የቁጥጥር ሥራውን አጠናክሮ መቀጠሉንም አስታውቋል።
