በዘንድሮው የበልግ ወቅት በሚኖረው ከፍተኛ ዝናብ ምክንያት በከተሞች የጎርፍ አደጋ ሊከሰት ስለሚችል አስፈላጊው ቅድመ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አሳሰበ።
በኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የትንበያ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አሳምነው ተሾመ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ በበልግ ወቅት ከሚኖረው ከፍተኛና ተደጋጋሚነት ያለው ከባድ ዝናብ የተነሳ በተለይም በቆላማ ስፍራዎችና በከተሞች ቅጽበታዊ ጎርፍ የመከሰት ዕድሉ ሰፊ ነው።
አዲስ አበባን ጨምሮ በደቡብና ምሥራቅ ትግራይ፣ በምሥራቅ አማራ፣ በአፋርና በመካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ የሆነ የዝናብ መጠን እንደሚጠበቅ ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል።
በተጨማሪም በሶማሌ ክልል ደቡባዊ ክፍል፣ በጉጂ፣ በቦረና፣ በሲዳማና በደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች እስከ 55 በመቶ የሚደርሰው ዓመታዊ የዝናብ መጠን የሚስተዋለው በዚህ ወቅት መሆኑን አሳምነው (ዶ/ር) አስረድተዋል።
የበልግ ዝናብ ተለዋዋጭነቱ እየጨመረ መምጣቱን የጠቀሱት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፤ ችግሩን ለመከላከል የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎችን ማከናወንና ኢንስቲትዩቱ የሚያወጣቸውን የትንበያ መረጃዎች በመጠቀም ቅድመ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል።
ጋዜጣ ኘላስ
