የተባበሩት መንግሥታት ለሰብዓዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር የሆኑት ቮልከር ተርክ በቅርቡ በፌደራል መንግሥቱ እና በትግራይ ኃይሎች መካከል የተከሰተውን ግጭት በሚመለከት ሁሉም ወገኖች ግጭትን ከማባባስ እንዲቆጠቡ አሳሰቡ።
ተርክ ማክሰኞ የካቲት 3/2018 ዓ.ም. ባወጡት መግለጫ ላይ በቅርቡ በፌደረል መንግሥቱ እና በትግራይ ክልል ኃይሎች መካከል የተከሰተው ግጭት በሰሜን ኢትዮጵያ አሳሳቢ የሆነውን የሰብዓዊ መብቶች እና የሰብዓዊ ሁኔታ ሁኔታ አደጋ ላይ የሚጥል ነው ብለዋል።
ተርክ እንዳሉት “ሁኔታው በጣም ተለዋዋጭ ነው፤ የበለጠ እየተባባሰ እንደሚሄድም እንሰጋለን፤ ይህም የክልሉን አደገኛ የሰብአዊ መብቶች እና የሰብዓዊ ሁኔታን ያባብሳል።”
አክለውም ሁለቱም ወገኖችበጦር መሣሪያ የታገዘ ግጭት ውስጥ ከመግባት ይልቅ በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በመታገዝ ውጥረቱን በፖለቲካዊ ውይይት እና በራስ መተማመንን ለማርገብ “የተቀናጀ እና ቀጣይነት ያለው ጥረት” ማድረግ እንደሚያስፈልጋቸው አሳስበዋል።
ከጥቂት ሳምንት በፊት የትግራይ እና የአማራ ክልሎች በይገባኛል በሚወዛገቡበት ጸለምት አካባቢ በህወሓት እና በፌዴራል መንግሥት መካከል ግጭት ተከስቶ የድሮን እና የከባድ መሣሪያ ጥቃት እንደነበር ተዘግቧል።
ተርክ በግጭቱ ወቅትም ሆነ ከግጭቱ በኋላ ሰላማዊ ዜጎች በሁለቱም ወገኖች በኩል በቁጥጥር መዋላቸውን መስማታቸው እንዳሳሰባቸው ገልጸዋል።
“ሰላማዊ ዜጎች ዳግም ውጥረቱ እየተባባሰ ባለበት ሁኔታ ውስጥ ዳግም ቅርቃር ገብተዋል” ያሉት ተርክ ለሁለቱም ወገኖች ጋር ግንኙነት አላችሁ በሚል የሚደረገው እስር “መቆም አለበት” ብለዋል።
ተርክ በቅርቡ በኢትዮጵያ እና በጎረቤት አገር ኤርትራመካከል የተፈጠረው ውጥረት አሳሳቢመሆኑን በመግለጽ፤ ሁኔታው እየተባባሰ የሚሄድ ከሆነ አገራቱ እንዲሁም በአፍሪካ ቀንድ ያሉ የሰብአዊ እና የሰብአዊ መብት ተግዳሮቶችን እንደሚያባብስ አስጠንቅቀዋል።
BBC Amharic
