ሳምንት በሆነው እስራኤል በኢራን ላይ በከፈተችው ጥቃት አሜሪካ ለመሳተፍ እጇን የምታስገባ ከሆነ “ሲኦል” ይከሰታል ሲሉ የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳዒድ ኻቲብዛዴህ ለቢቢሲ ተናገሩ።
አሜሪካ በኢራን ላይ በሚካሄደው ጥቃት የምትሳተፍ ከሆነ ኢራን ሁሉንም አማራጮች በጠረጴዛዋ ላይ መሆናቸውን በማመልከት “ይህም አጠቃላይ ቀጣናውን አረንቋ እና ሲኦል ያደርገዋል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።
ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሳዒድ ኻቲብዛዴህ ለቢቢሲ እንደተናገሩት አሁንም ኢራን ዲፕሎማሲያዊ መፍትሔ ምርጫዋ መሆኑን በመጥቀስ፤ ነገር ግን ጥቃቱ በኢራን ላይ የሚቀጥል ከሆነ “ማንም ወደ ድርድር ሊሄድ አይችልም” ብለዋል።
ይህ ጦርነት “የአሜሪካ ጦርነት አይደለም” ያሉት ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፣ “ትራምፕ የሚሳተፉ ከሆነ ግን በማያገባቸው ጦርነት የተሳተፉ ፕሬዝዳንት ሆነው እንደሚታወሱ ተናግረዋል።
“እኛ የምናስበው ይህ ጦርነት አሜሪካንን የሚመለከት ጦርነት አይደለም፤ ነገር ግን ወደ ጦርነቱ መግባት የሚፈልጉ ከሆነ፣ ትራምፕ ለዘላለሙ ወደ ማይመለከታቸው ጦርነት ተጎትተው የገቡ መሪ ተብለው ሲታሰቡ ይኖራሉ” ብለዋል።
በዋናነት የኢራንን የሚሳዔል እና የኒውክሌር ተቋማትን ዒላማ አድርጋ ጥቃቶችን በመፈጸም የሰነበተችው እስራኤል ከመሬት በታች የሚገኙ ያለቻቸውን የኒውክሌር ተቋማትን ለማውደም የአሜሪካን ድጋፍ እየጠየቀች ነው።
ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እስካሁን ኢራንን ለማጥቃት ከእስራኤል ጋር እንደሚያብሩ የሚያመለክት ግልጽ ምላሽ ባይሰጡም፤ በኢራን ላይ የሚፈጸም ጥቃትን ማጽደቃቸውን በተመለከተ የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን እየዘገቡ ነው።
BBC amharic
