ኢትዮጵያ ምርቶቿን ከቀረጥ ነጻ በሆነ ሥርዓት ወደ አፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ማዕቀፍ አባል ሀገራት መላክ እንደምትጀምር የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር አስታወቀ።
ሚኒስቴሩ ይሄን ያስታወቀው ለዓለም የንግድ ድርጅት አባልነት በስዊዘርላንድ ጄኔቫ የተደረገውን ስድስተኛ ዙር የሥራ ቡድን ስብሰባ በተመለከተ ለመገናኛ ብዙኃን መስከረም 19 ቀን 2018 ዓ.ም በሰጠው መግለጫ ነው።
መግለጫውን የሰጡት የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)፤ መስከረም 29 ኢትዮጵያ አህጉራዊ ነፃ የሸቀጦች ንግድ ትግበራን በይፋ ታስጀምራለች ሲሉ ተናግረዋል።
በዚህም ኢትዮጵያ በሚቀጥለው ሳምንት ወደ አፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ማዕቀፍ አባል ሀገራት ለመጀመሪያ ጊዜ ምርቷን ከቀረጥ ነፃ መላክ ትጀምራለች ያሉት ሚንስትሩ ይህም የንግድ ተወዳዳሪነትን እንደሚጨምር ተናግረዋል።
ከዚህ ቀደም ኢትዮጵያ ወደ ኬኒያ በቆሎ እና ቦለቄ 15 በመቶ ቀረጥ ከፍላ እንደምትልክ ለአብነት ያነሱት ሚኒስትሩ፤ ነገር ግን የመጀመሪያውን ጭነት ካስጀመረች በኋላ ወደ ኬኒያ የምትልከው ሸቀጥ ከቀረጥ ነጻ እንደሚሆን አመልክተዋል።
በተጨማሪም የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጠና ስምምነት ትግበራ ከንግድ ቀጠናነት ባሻገር የአፍሪካ ዘላቂ ዕድገትን ለማረጋገጥ የጎላ ጠቀሜታ እንደሚኖረው መግለፃቸውን የዘገበው ኢፕድ ነው።
