የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ከኢራን ጋር አዲስ የሰላም ስምምነት ለመፍጠር ጥረት ቢጀምሩም፣ የእስራኤል ከፍተኛ ባለሥልጣናት ግን ድርድሩ ስኬታማ ይሆናል የሚል እምነት እንደሌላቸው ገለጹ።
ምንም እንኳን ትራምፕ ለስምምነቱ ከፍተኛ ቁርጠኝነት ቢያሳዩም፣ እስራኤል ግን ኢራን ለድርድር የምትቀርብበትን ፍላጎት በጥርጣሬ እንደምትመለከተው ለሮይተርስ አስታውቃለች።
በአሁኑ ወቅት በኢራን እና በእስራኤል መካከል ያለው የጦርነት ውጥረት በከፍተኛ ደረጃ በቀጠለበት ሁኔታ፣ ፕሬዝዳንት ትራምፕ የኢራን ባለሥልጣናት ወደ ስምምነት እንዲመጡ የአምስት ቀናት ቀነ-ገደብ አስቀምጠዋል።
ይህ ማስጠንቀቂያ ተግባራዊ ካልሆነ አሜሪካ በኢራን ላይ “ከባድ ጥቃት” እንደምትሰነዝር የዛተች ሲሆን፣ ይህም በቀጠናው ያለውን ስጋት ይበልጥ አባብሶታል።
በዚህ ሳምንት በፓኪስታን ይካሄዳል ተብሎ በሚጠበቀው የሁለቱ ሀገራት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ስብሰባ ላይ፣ አሜሪካ በኢራን የኒውክሌር እና የባሊስቲክ ሚሳዔል መርሃ-ግብሮች ላይ ጠንካራ ማዕቀብ እንዲጣል ትፈልጋለች።
ሆኖም ስማቸው ያልተጠቀሰ የእስራኤል ባለሥልጣናት ኢራን እነዚህን የአሜሪካ ጥያቄዎች ተቀብላ ከስምምነት ትደርሳለች የሚል ተስፋ እንደሌላቸው በድጋሚ አረጋግጠዋል።
