በትግራይ ክልል የሚገኙ መምህራንና የመንግስት ሰራተኞች የተከለከለውን ደመወዛቸውን ለማስመለስና ድምፃቸውን ለማሰማት፣ መጋቢት 15 ቀን 2018 ዓ.ም በሁሉም የክልሉ ከተሞች ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚካሄድ ተገለጸ።
ይህ ሰልፍ የሚዘጋጀው በክልሉ ትምህርት ቢሮ፣ በመምህራን ማህበርና በተማሪ ወላጆች ማህበር ትብብር መሆኑ ታውቋል።
የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ኪሮስ ጉዕሽ እንደገለጹት፣ አሁን በስራ ላይ ያለው የደመወዝ ክልከላ በትግራይ ህዝብ ላይ የተፈጸመው የዘር ማጥፋት ድርጊት ቀጣይ አካል ነው።
ኃላፊው አክለውም፣ ድርጊቱ ሆን ተብሎ የትግራይ ትውልድ እንዳይማር፣ ህዝቡም ተስፋ ቆርጦ እንዲበተንና እንዲጠፋ የታቀደ ስራ በመሆኑ፣ ይህንን ግፍ ለዓለም ማህበረሰብ ለማሳወቅ ሰልፉ አስፈላጊ ሆኗል ብለዋል።
የመምህራን ማህበር ፕሬዝዳንት መምህር ንግስቲ ጋረድ በበኩላቸው፣ መምህራን ላለፉት 16 ወራት ደመወዝ ሳይከፈላቸው በትዕግስት ሲያስተምሩ መቆየታቸውን አስታውሰዋል።
ሆኖም ግን ያለ ምንም ምክንያት ደመወዛቸው በድጋሚ መከልከሉ በከፍተኛ ችግር ውስጥ እንዲወድቁ ማድረጉን ጠቁመው፣ ይህ ኢ-ፍትሃዊ ድርጊት ይቆም ዘንድ በሰላማዊ ሰልፉ ድምፃቸውን እንደሚያሰሙ ገልጸዋል።
የወላጆች ማህበር ፕሬዝዳንት መምህር ከላሊ ፀጋይም በበኩላቸው፣ መምህራን ሳይበሉ ማስተማር ባለመቻላቸው የተማሪዎች የመማር መብት መጣሱን ገልጸው፣ ዓለም አቀፍ ተቋማት ለችግሩ መፍትሄ እንዲያመጡ ጥሪ አቅርበዋል።
