የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ሚዛን አማን ከተማ የሚያደርገውን የቅድመ ምረቃ በረራ ሐምሌ 3 ቀን 2018 ዓ.ም በይፋ የጀመረ ሲሆን ፣ የመጀመሪያው ታሪካዊ በረራም በሚዛን አማን አውሮፕላን ማረፊያ በሰላም ማረፉ ተገልጿል።
አየር መንገዱ ወደ ከተማዋ በሳምንት ሦስት ጊዜ የሚያደርገው ይህ አዲስ የበረራ አገልግሎት፣ ለደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በተለይም ለቤንች ሸኮ ዞን ነዋሪዎች ዘመናዊና ምቹ የጉዞ አማራጭን ይዞ የመጣ ነው።
አገልግሎቱ በአካባቢው ያለውን የንግድ፣ የቱሪዝም፣ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ትስስር እንቅስቃሴዎችን በጥልቀት እንደሚያጠናክርና አዳዲስ የልማት ዕድሎችን እንደሚፈጥር ተገልጿል።
ይህንን የመጀመሪያ በረራ አስመልክቶ በአውሮፕላን ማረፊያው በተዘጋጀው ደማቅ የአቀባበል መርሃ ግብር ላይ የክልሉ፣ የዞኑና የከተማዋ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል።
የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊና ዋና የመንግሥት ተጠሪ አቶ ፍቅሬ አማን የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳዳሪና አቶ ሀብታሙ ካፍትን የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ከንቲባ **ኢንጂነር ሰለሞን ሌዊን እንዲሁም የሀገር ሽማግሌዎች፣ ታዋቂ ግለሰቦችና በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች በሥፍራው ተገኝተው ሂደቱን ተከታትለዋል።
በአየር ማረፊያው የተከናወነው ይህ ታሪካዊ የአቀባበል ሥነ-ሥርዓት በአካባቢው ብሔረሰቦች ውብ ባህላዊ ጭፈራዎች፣ ማራኪ ትርኢቶችና በደማቅ የህዝብ እልልታ የታጀበ እንደነበር ተገልጿል።
በአቀባበሉ ላይ የተገኙት የአካባቢው ነዋሪዎች፤ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎቱ መጀመር ለአካባቢው ሁለንተናዊ ዕድገትና ለኢንቨስትመንት መነቃቃት የሚጫወተው ሚና የላቀ መሆኑን በመግለጽ የተሰማቸውን ከፍተኛ ደስታና ምስጋና አቅርበዋል።
ይህ አዲስ የበረራ መስመር መከፈት ሚዛን አማንን ከዋና ከተማዋና ከሌሎች የአገሪቱ ክፍሎች ጋር ይበልጥ የሚያገናኝ በመሆኑ፣ ለአካባቢው የኢኮኖሚ እድገት አዲስ ምዕራፍ የከፈተ ክስተት ተብሎ ተወድሷል።
