ዩናይትድ ስቴትስ በግጭት፣ በአየር ንብረት ለውጥ እና በኢኮኖሚ አለመረጋጋት ሳቢያ ለከፍተኛ የምግብ እጥረት ለተጋለጡ በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ሰዎች ድጋፍ የሚውል የ93 ሚሊዮን ዶላር የድንገተኛ የምግብ እርዳታ መርሐ ግብር ማድረጓን አስታወቀች።
ይህ የገንዘብ ድጋፍ የተደረገው፣ ቀደም ሲል የዓለማችን ትልቁ የእርዳታ ኤጀንሲ የነበረው የዩ.ኤስ.ኤይ.ዲ ኤጀንሲ በትራምፕ አስተዳደር በወጣው ወጪ ቆጣቢ ማሻሻያ ምክንያት ከተዘጋ በኋላ ነው።
የዚህ እርዳታ ዋና አላማ በአፍሪካ ውስጥ እየተባባሰ የመጣውን የረሀብ ችግር ለመቋቋም የተባለ ሲሆን የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደገለፀው ፣ ይህ ገንዘብ 1,209 ሜትሪክ ቶን የምግብ ክምችት እና ተጨማሪ 11,285 ሜትሪክ ቶን ለህጻናት የሚውል የህክምና ምግብ ለማምረት የሚያስችል ነው። በአጠቃላይ፣ ወደ አንድ ሚሊዮን የሚጠጉ ህጻናት በዚህ እርዳታ እንደሚጠቀሙ ይጠበቃል።
በተጨማሪም የ93 ሚሊዮን ዶላር የእርዳታ ፓኬጁ ከኢትዮጵያ በተጨማሪ ማሊ፣ ኒጀር፣ ሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን፣ ናይጄሪያ፣ ማዳጋስካር፣ የመካከለኛው አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ጂቡቲ፣ ኬንያ፣ ቻድ እና ሃይቲን ያጠቃልላል።
