በአሁኑ ወቅት ዓይነት 1 በሚባለው የስኳር ህመም በርካታ ህፃናትና ወጣቶች ተጋላጭ እየሆኑ መምጣታቸውን የኢትዮጵያ ስኳር ህሙማን ማህበር አስታውቋል።
የማህበሩ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ኤርሚያስ ገ/ማርያም በነበራቸዉ ቆይታ እንደገለጹት ህመሙ በአብዛኛው በህፃናትና በወጣቶች ዘንድ ጎልቶ ይታያል። ቀድሞ ካልታወቀና ተገቢውን ህክምና ማድረግ ካልተቻለ ከባድ የጤና ችግሮችን ያስከትላል፡፡
ዓይነት አንድ የሚባለው የስኳር ህመም የሚከሰተው የሰውነት መከላከያ ሥርዓት በፓንክሪያስ ውስጥ ኢንሱሊን የሚያመነጩ ሴሎችን በማጥቃት ነው።
በዚህም ምክንያት ሰውነት በቂ ኢንሱሊን ማምረት ስለማይችል በደም ውስጥ የሚገኘው የስኳር መጠን እንዲጨምርና ህመሙ እንዲከሰት ያደርጋል።ይህ ህመም በተለይም በህፃናት እና እድሜያቸው ከ30 ዓመት በታች በሆኑ ሰዎች ላይ ይከሰታል።
ከፍተኛ የውሃ ጥም፣ቶሎ ቶሎ ዉሃ ሽንት መሽናት፣ የመራብ ስሜት ፣ድካም ፣ ከፍተኛ የሆነ ክብደት መቀነስ ከህመሙ ምልክቶች መካከል ይገኙበታል።
ወላጆችና አሳዳጊዎች እነዚህን ምልክቶች በልጆቻቸው ላይ ሲያስተውሉ በአፋጣኝ ወደ ጤና ተቋማት በመውሰድ ምርመራ ሊያደርጉ ይገባል። በተጨማሪም ዓይነት ሁለት በመባል የሚታወቀው የስኳር ህመም ከዓይነት አንድ የስኳር ህመም የሚለይ መሆኑ ተነግሯል።
ሰዎች በአጋጣሚ ለሌላ ምርመራ ሄደው ድንገት በሽታው እንዳለባቸው ሊረዱ ይችላሉ የተባለ ሲሆን የህመሙ ምልክት ሳይታይ ረጅም ጊዜ ሊቆይ እንደሚችል ተገልጿል።
ህመሙን አስቀድሞ መለየትና ተገቢ ክትትል ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ኤርሚያስ በህፃናትና በወጣቶች ጤና ላይ የሚደርሱ አደገኛ ተጽዕኖዎችን ለመቀነስ ወሳኝ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
ከብሰራት ሬዲዮ
