ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የቻይናው ባይት ዳንስ የቲክቶክን ድርሻ እንዲሸጥ ከኩባንያው ጋር የተጀመረው ድርድር መተግበሪያው ከፊታችን ቅዳሜ በኋላ በሀገረ አሜሪካ ከመታገዱ በፊት በስምምነት ፊርማ እንደሚጠናቀቅ አመላክተዋል።
ትራምፕ ቲክቶክ ቻይናዊ ያልሆነ ገዢ እንዲያፈላልግ እስከ ቅዳሜ ኤፕረል 5 ቀን ቀነ-ገደብ አስቀምጠዋል። ይህ ካልሆነ ግን ከብሔራዊ ደህንነት ጋር በተያያዘ መተግበሪያው በሀገረ አሜሪካ እገዳ እንደሚጣልበት አስጠንቅቀዋል።
ፕሬዚዳንቱ እሁድ ዕለት ጉዳዩን ለጋዜጠኞች ሲያብራሩ፥ “አቅሙ ያላቸው በርካታ ገዢዎች አሉን፣ ለቲክቶክ ከፍተኛ ፍላጎት አለ፤ ቲክቶክ በአሜሪካ ሕያው ሆኖ መቀጠሉን ማየት እፈልጋለሁ” ብለዋል።
170 ሚሊዮን አሜሪካውያን የሚጠቀሙበት የአጭር ቪዲዮ መተግበሪያ የቲክቶክ የድርሻ ሽያጭ ስምምነት እንዲሳካ ቻይና ለምትጫወተው ሚና እንደ ማበረታቻ የታሪፍ ቅናሽ ሊያደርጉላት እንደሚችሉም ተናግረዋል።
