ኢቲ ኦንላይን ኮሌጅ ለሁለተኛ ዙር በድህረ ምረቃ ፕሮግራሞች ሲያሰለጥናቸው የቆዩ 25 ወንዶችና 10 ሴቶች በአጠቃላይ 35 ተማሪዎችን በዛሬው ዕለት አስመርቋል።
በኦንላይን ትምህርት በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነው ኢቲ ኦንላይን ኮሌጅ (ET Online College) በመጋቢት 24 ቀን 2013 ዓ.ም ከትምህርትና ስልጠና ባለስልጣን በኦንላይን (በበየነ መረብ) ትምህርት አሰጣጥ ዘዴ የመጀመሪያ በመሆን የዕውቅና ፈቃድ አግኝቶ ወደ ሥራ መግባቱን የኮሌጁ መስራችና ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሀብታሙ መለሰ ተናግረዋል።
በዛሬው ዕለትም በሁለት የድህረ ምረቃ ኘሮግራሞች ማለትም በማስተርስ ኦፍ ቢዝነስ አድሚኒስትሬሽን (MBA) እና በዴቬሎፕመንት ኢኮኖሚክስ (MSc) ለሁለተኛ ጊዜ ተማሪዎችን ማስመረቁን ገልጸዋል።
ተመራቂ ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ በበየነ መረብ (Online) የሁለተኛ ዲግሪያቸውን ያገኙ ሲሆን፤ መንግሥት ባዘጋጀው የትምህርት ፍኖተ ካርታ የታገዘ የድህረ ምረቃ ትምህርታችውን በሚያመቻቸው ሰዓትና ቦታ ሆነው ሲማሩ የቆዩ መሆናቸውን አንስተዋል።
በዚህም መሠረት “የኦንላይን ቴክኖሎጂን በመጠቀም የትምህርት ተደራሽነትን ለማስፋፋት እና ጥራት ያለውን ትምህርት አመቺ በሆነ መንገድ ለማቅረብ የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ የበኩሉን ድርሻ በማበርከትና በመወጣት ላይ ይገኛል” ብለዋል።
ኢትዮጵያ የምትፈልገውን የሰለጠነ የሰው ኃይል በብቃትና በጥራት እንዲያስተምር ችግር ፈቺ የሆኑ ጥናትና ምርምሮችን በማድረግ ጥራት ያለው አገልግሎት ለማህበረሰቡ እንዲሰጥ መቋቋሙን ያነሱት የኮሌጁ መስራችና ፕሬዝዳንት፤ ይህም ሌሎች ባለሀብቶች ወደዚህ የሥራ ዘርፍ እንዲገቡ ለማድረግ የሚያግዝ መሆኑን ተናግረዋል።
ኮሌጁ ከሀገር ውስጥ በተጨማሪ በርከት ካሉ በአሜሪካን ሀገር እውቅና ካላቸው የትምህርት ተቋማት ጋርም የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሞ በትብብር እየሰራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።
ከተለያዩ ሀገራት በሚመጡ መምህራን ጋር ልምድ ልውውጥ በማድረግ በተለይም ተማሪዎች ዓለም አቀፍ እውቀትን እንዲጨብጡና በሚሰማሩበት የሥራ ዘርፍ ስኬታማ እንዲሆኑ ለማስቻል የተለያዩ ሥራዎች ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል።
ከዚህ በተጨማሪም አጫጭር ስልጠናዎችን እና ኮርሶችን ሙሉ በሙሉ በኦንላይን መንገድ በቢዝነስ እና ኢኮኖሚክስ፣ በሊደርሽፕ፣ በቴክኖሎጂ ፣ በኢንጅነሪንጅ እና ጤና እያቀረበ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።
(አሐዱ ሬዲዮ)
